በግዛቷ ውስጥ የሚገኘው የዓለም ትልቁ የተፈጥሮ ጋዝ ማምረቻ ስፍራ በእስራኤል የተመታባት ኢራን፤ የኳታር የነዳጅ ኩባንያ ላይ የሜሳዔል እና የሮኬት ጥቃቶችን ፈጸመች።
ይህንን ጥቃት ተከትሎ ኳታር ኢራንን “ለቀጣናው ብሔራዊ ደኅንነት እና መረጋጋት ቀጥተኛ ስጋት” ስትል የገለጸች ሲሆን ሁለት የቴህራን ዲፕሎማቶችንም አባርራለች።
ትናንት እስራኤል ደቡብ ፓርስ የሚገኘው የፔትሮኬሚካል ተቋም የአየር ድብደባ ከፈጸመች በኋላ ኢራን፤ ኳታር፣ ሳዑዲ አረቢያ እና የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ውስጥ የሚገኙ የነዳጅ ማውጫ ስፍራዎች ላይ የአጸፋ ጥቃት እንደምትፈጽም አስጠንቅቃ ነበር።
የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን ደቡብ ፓርስ የጋዝ ስፍራ ላይ ከደረሰው ጥቃት በኋላ ባደረጉት ንግግር የዚህ ጥቃት “መዘዝ ከቁጥጥር ውጪ” እንደሚወጣ አሳስበዋል።
ምሽት ላይ በኳታር ‘ራስ ላፋን ኢንዱስትሪያል’ ከተማ ውስጥ የሚገኘው ዋነኛ የነዳጅ ማቀነባበሪያ ስፍራ በሚሳዔሎች እንደተመታ በአገሪቱ መንግሥት ባለቤትነት የተያዘው ‘ኳታር ኢነርጂ’ ኩባንያ አስታውቋል። በጥቃቱ የተነሳ ስፍራው በእሳት እንደተያያዘ እና ተቋሙ ላይ “ከፍተኛ ጉዳት” እንደደረሰም ገልጿል።
ኩባንያው ዛሬ ንጋት ባወጣው መረጃ ደግሞ ኢራን በፈጸመችው ሌላ የሚሳዔል ጥቃት የኢነርጂ ተቋሙ ላይ ጉዳት መድረሱን አስታውቋል።
ኳታር የኢራንን ጥቃት “ለቀጣናው ብሔራዊ ደኅንነት እና መረጋጋት ቀጥተኛ ስጋት” ስትል ገልጻዋለች። “የኢራን ወገን ቀጠናውን ወደ ገደል የሚወስደው እና የዚህ ቀውስ አካል ያልሆኑ አገራትን ወደ ግጭት አዙሪት የሚስበውን የማባባስ ፖሊሲ ቀጥሎበታል” ብላለች።
“ምላሽ የመስጠት መብት እንዳላት” የገለጸችው ኳታር፤ “ሉዐላዊነቷን፣ ደኅንነቷን እና የዜጎቿን ደኅንነት ለማስጠበቅ አስፈላጊውን እርምጃ በሙሉ ከመውሰድ ወደ ኋላ እንደማትል” አስጠንቅቃለች።
ከሰዓታት በኋላም ኳታር ሁለት የኢራን ዲፕሎማቶች በ24 ሰዓት ውሰጥ አገሪቱን ለቅቀው እንዲወጡ አዝዛለች። ለቅቀው እንዲሄዱ የታዘዙት የኢራን ወታደራዊ እና የደኅንነት አታሼዎች እንደሆኑ የኳታር ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል።
BBC
