በሕንድ ዴልሂ እየተካሄደ ባለው የ2026 የኤ አይ ዓለም አቀፍ ጉባኤ ላይ የተገኙት የቀድሞው የእንግሊዝ የፋይናንስ ሚኒስትር እና የአሁኑ የኦፕን ኤ አይ (OpenAI) ከፍተኛ የሥራ ኃላፊ ጆርጅ ኦስቦርን፣ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስን የማይቀበሉ ሀገራት ብሔራዊ ውድቀት እንደሚጠብቃቸው አስጠንቅቀዋል።
ኦስቦርን እንዳሉት፣ ይህንን የቴክኖሎጂ አብዮት ለመጠቀም የማይፈቅዱ ሀገራት ደካማና ድሃ ሆነው ከመቅረታቸውም በላይ፣ የሰለጠነ የሰው ኃይላቸው የተሻለ ዕድል ፍለጋ አገሩን ጥሎ ይሰደዳል።
በአሁኑ ወቅት ዓለም በአሜሪካው ኦፕን ኤ አይ እና በቻይና የኤ አይ ቴክኖሎጂዎች መካከል መከፈሏን የጠቀሱት አመራሩ፣ ሀገራት ከሁለቱ አንዱን ለመምረጥ መገደዳቸውንና ወደ ኋላ መቅረት የከፋ ጉዳት እንደሚያስከትል ገልጸዋል።
ዘ ጋርዲያንን ዋቢ አድርጎ የወጣው ይህ ዘገባ እንደሚያመለክተው፣ ብዙ ሀገራት በሌሎች ቴክኖሎጂዎች ላይ ጥገኛ መሆን ቢያሰጋቸውም፣ ሳይጠቀሙ መቅረት ግን የከፋ ብሔራዊ ውድቀትን እንደሚያስከትልባቸው ኦስቦርን አስረድተዋል።
የቴክኖሎጂው ሽሚያ በከፍተኛ ሁኔታ በጨመረበት በዚህ ወቅት፣ ሀገራት በኤ አይ ዘርፍ ኢንቨስት ካላደረጉና አሠራራቸውን ካላዘመኑ ከዓለም አቀፉ የኢኮኖሚና የዕውቀት መድረክ ተገልለው እንደሚቀሩ ተመልክቷል። ይህ ማስጠንቀቂያ በተለይ በማደግ ላይ ያሉ ሀገራት በቴክኖሎጂው ረገድ ያላቸውን አቋም ዳግም እንዲፈትሹ የሚያደርግ መሆኑም ተገልጿል።
