በኢትዮጵያ የምግብና መድኃኒት ባለስልጣን የወጣውና በፍትህ ሚኒስቴር የጸደቀው “የሕክምና ጋዝ ማምረቻ ተቋማት ቁጥጥር መመሪያ ቁጥር 1061/2017″ለሕክምና አገልግሎት የሚውሉ ጋዞችን በተለይም ኦክስጅንን የሚያመርቱ ተቋማት ጥራትና ደህንነት ቁጥጥር ሥር እንዲውሉ አስችሏል።
የመመሪያው ዋና ዓላማ የሕክምና ጋዞች ደህንነታቸው የተጠበቀ ጥራታቸው የተረጋገጠ እና ውጤታማ መሆናቸውን በማረጋገጥ የታካሚዎችን ጤንነት መጠበቅ ነው።
ይህ መመሪያ በሕክምና ጋዞች ላይ በካይ ነገር እንዳይኖር በመከላከል በታካሚዎች ላይ ሊደርስ የሚችል የጤና ችግር እና አሉታዊ ክስተቶችን ለመቀነስ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ተገልጿል።
መመሪያው የጥራት ደረጃውን የጠበቀ የመድኃኒት ጋዝ ለታካሚዎች ለማቅረብ የሚያስችሉ መስፈርቶችን ያካተተ ሲሆን እነዚህም ጋዞችን በማምረት በጥራት ቁጥጥር በማከማቸትና በማሰራጨት ላይ ተግባራዊ የሚደረጉ ናቸው ተብሏል።
የሕክምና ጋዞች በተለይም ኦክስጅን ከፍተኛ ፍላጎት ያላቸው በመሆናቸው ምርታቸው አስፈላጊውን የጥራት መመዘኛ ማሟላቱን ማረጋገጥ ወሳኝ መሆኑ በዚሁ መመሪያ ተመላክቷል።
የምርቶቹ ባህሪ እና በማምረት ሂደት ውስጥ የሚያስፈልገው ልዩ መሳሪያ የሕክምና ጋዝ ደህንነትን ጥራትንና ውጤታማነትን ለማረጋገጥ ወጥና ተከታታይ የሆነ የማስፈጸሚያ ሥርዓት መዘርጋት አስፈላጊ ማድረጉ ለመመሪያው መውጣት ተጨማሪ ምክንያት መሆኑ ተጠቁሟል።
CapitalNews
