የዓለም አከርካሪ ቀን (World Spine Day) “አከርካሪዎ ላይ ኢንቨስት ያድርጉ” በሚል መሪ ቃል በዛሬው ዕለት በተለያዩ የግንዛቤ ማስጨበጫ ኹነቶች የተከበረ ሲሆን፤ መሰል ዝግጅቶች በአከርካሪ ህመም መንስኤዎችና መከላከያዎች ዙሪያ ግንዛቤ ለመፍጠርና ንቃተ ህሊናን ለማሳደግ ወሳኝ እንደሆኑ ተነግሯል፡፡
ቀኑን አስመልክቶ በተሰራጨ መረጃ ላይ እንደተገለጸው፣ በዓለማቀፍ ደረጃ ወደ አንድ ቢሊዮን የሚገመቱ ሰዎች በአከርካሪ ህመምና የአካል ጉዳት የሚሰቃዩ ሲሆን፤ በዋናነትም የጉልበት ሥራዎች፣ ያልተስተካከለ አቀማመጥ፣ ለረዥም ጊዜ ሳይንቀሳቀሱ መቆየት እንዲሁም ከመጠን ያለፈ ውፍረት የተለመዱ የበሽታው መንስኤዎች ናቸው፡፡
በኢትዮጵያም ውሃና ማገዶ አዘውትረው የሚሸከሙ ሰዎች፣ ቢሮ ውስጥ ረጅም ሰአት ተቀምጠው የሚሰሩ እንዲሁም የግንባታ ሠራተኞች በአብዛኛው አከርካሪ አጥንታቸው ለአደገኛ ከባድ ጭነት እንደሚዳረግ የጠጠቆመ ሲሆን፤ በተለይም በገጠር አካባቢ ምንም ዓይነት የአከርካሪ አጥንት አጠባበቅ ግንዛቤ ባለመኖሩ ችግሩ የከፋ ነው ተብሏል፡፡
በሳፋየር ሆቴል በተዘጋጀው የዓለም አከርካሪ ቀን መርሃ ግብር ላይ በጉዳየ ዙሪያ ማብራሪያ የሰጡ የዘርፉ ባለሙያ፣ ማህበራዊ ሚዲያ ላይ አቀርቅረው የሚውሉ ሰዎችም ለአከርካሪ አጥንት ህመም ተጋላጭ መሆናቸውን አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል፡፡ ለረዥም ሰዓት አቀርቅሮ ማህበራዊ ሚዲያ ከመጠቀም መታቀብ እንደሚያስፈልግም ባለሙያው መክረዋል፡፡
በኢትዮጵያ ለ11ኛ ጊዜ የተከበረውን የዓለም አከርካሪ ቀን መርሃ ግብር ያዘጋጀው “ፈርስት ስፓይን ክሊኒክ”፣ ከ24 ዓመታት በላይ በአከርካሪ አጥንት ህክምና ላይ በማተኮር ሲሰራ የቆየ ተቋም ሲሆን፤ በተጨማሪም የተለያዩ የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረኮችን በማዘጋጀትና ማህበረሰቡን በማስተማር ይታወቃል፡፡
