የኢትዮጵያ እና ቻይናን የሚዲያ ትብብር ለማሳደግ ያለመ መድረክ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተካሂዷል።
በመድረኩ የመንግስት ኮሚኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ለገሰ ቱሉ (ዶ/ር) እና የቻይና ሬድዮ እና ቴሌቭዥን አስተዳደር ሚኒስትር ሳዎ ዡሚን እንዲሁም ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተውበታል።
የመንግስት ኮሚኒኬሽን አገልግሎት ሚንስትር ለገሰ ቱሉ ዶ/ር የሚዲያ ትብብርን ወደ ስልጠና በማሳደግ ብቃት እና ስነ-ምግባር ያላቸው የሚዲያ ባለሞያዎችን ለማፍራት በጋራ መስራት ይገባል ብለዋል።
የሁለቱን ሀገራት ህዝብ ሊያስተሳስሩ የሚችሉ ተግባቦቶችን በማጠናከር እና ምቹ የሆነ ከባቢን በመዘርጋት የሚዲያውን ዘርፍ ጥቅም ማሳደግ እንደሚጠበቅም ገልፀዋል ሚኒስትሩ።
ኢትዮጵያ እና ቻይና በባህል እና ታሪክ ረጅም ዓመታት ያስቆጠሩ ሀገራት ናቸው ያሉት የቻይና ሬድዮ እና ቴሌቭዥን አስተዳደር ሚኒስተር ሳዎ ዡሚን፥ ቻይና ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ትብብር እና ትስስር ለማጠናከር በትኩረት እንደምትስራ ተናግረዋል።
በየጊዜው እያደገ ባለው የተሳሰረ ዓለም ውስጥ ሚዲያ እንደ ድልድይ ነው፤ በባህልና ታሪክ ሀብታም የሆኑትን ኢትዮጵያ እና ቻይናን ለማስተሳሰር ሚዲያው ከፍተኛ ሚና አለው ሲሉ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ምክትል ሥራ አስፈፃሚ ዘላለም እንዳሻው ገልፀዋል።
ምክትል ሥራ አስፈፃሚው እንዳሉት የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ይሄን ሚናውን በሚገባ እየተወጣ ይገኛል ብለው፤ በቀጣይም የሀገራቱን የሚዲያ ስራ የሚያስተዋውቁ እና የህዝብ ለህዝብ ትስስርን የሚያጠናክሩ ስራዎች የመስራቱን ተግባር ሚዲያው አጠናክሮ እንደሚቀጥል ጠቁመዋል።
