በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የባህልና ኪነ-ጥበብ ቢሮ እና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ትብብር የተዘጋጀው ልዩ የውይይት መድረክ፣ “የወጣቶች ተሳትፎ በልሳነ-ብዙ የትምህርት ስርዓት ለኢትዮጵያ ብልጽግና” በሚል መሪ ቃል በአንጋፋው ዩኒቨርሲቲ ተካሂዷል።
በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ26ኛ፣ በሀገራችን ደግሞ ለ3ኛ ጊዜ የተከበረው ይህ ዕለት፤ ኢትዮጵያ የበርካታ ቋንቋዎችና ባህሎች ባለቤት መሆኗን በማጉላት፣ ለዘርፉ ዘላቂ ዕድገት ከምሁራን ጋር በጋራ ለመስራትና ጠንካራ የፖሊሲ ድጋፍ ለማድረግ ያለመ መሆኑ ተገልጿል።
በመድረኩ ላይ የምልክት ቋንቋን በትምህርት ሥርዓት ውስጥ ማካተትን ጨምሮ የኢትዮጵያ የቋንቋ ሥርዓተ-ትምህርት ታሪካዊ ጉዞ ላይ ያተኮሩ ጥናታዊ ጽሁፎች ቀርበው ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸዋል።
የባህል ዘርፍ ም/ቢሮ ኃላፊ አቶ አዲሱ ሻንቆ ባስተላለፉት መልዕክት፣ ቋንቋ ባህልና እሴቶቻችንን የምንገልጽበት ትልቅ ሀብትና ውበታችንን የምናሳይበት ድልድይ መሆኑን ገልጸው፣ መንግስት ለዘርፉ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን አረጋግጠዋል።
መድረኩ በልሳነ-ብዙ ትምህርት ዙሪያ ያሉ ተግዳሮቶችን በመለየትና ለወደፊት የሥራ አቅጣጫዎች ጠቋሚ የሆኑ ሃሳቦችን በማንሳት በስኬት ተጠናቋል። ይህ መሰል መድረክ የሀገራችንን ብዝሃነት እንደ አንድ ትልቅ አቅም በመጠቀም ለጋራ ብልጽግና የምናደርገውን ጉዞ የሚያፋጥን መሆኑ ተመላክቷል።
