የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር 50ኛውን ዓለም አቀፍ የሴቶች ቀን (ማርች 8) ምክንያት በማድረግ፣ ሙሉ በሙሉ በሀገር ውስጥ ግብዓትና በኢትዮጵያዊት ተመራማሪ የተሰራ የንፅህና መጠበቂያ ሞዴስ “ለአንድ ልብ ለትውልድ” የበጎ አድራጎት ድርጅት በስጦታ አበርክቷል።
የሚኒስቴር ዴኤታው አቶ ታረቀኝ ቡሉልታ በወቅቱ እንደገለጹት፣ ተቋሙ ብቁና ጤናው የተጠበቀ አምራች ዜጋ ለመፍጠር በሚያደርገው ጉዞ የሴቶች ሚና የላቀ ነው። በመሆኑም ሴት አምራቾችን የመደገፍና የማብቃት ስራ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።
ስጦታ የተበረከተው የንፅህና መጠበቂያ ምርት በሚኒስቴሩ ሴት ተመራማሪዎች ጥናትና ምርምር የተሰራ መሆኑ፣ ተቋሙ ለሴቶች ሙያዊ እድገትና ለሀገር በቀል ቴክኖሎጂ የሰጠውን ትኩረት በተግባር ያሳየበት ክስተት ሆኖ ተመዝግቧል።
የምርቱ ፈጣሪ ረዳት ተመራማሪ ፋይዳ ሸምሱ በበኩሏ፣ የተቋሙን የምርምር መሰረተ ልማቶች በመጠቀም በዘርፉ የሚታዩ ችግሮችን ለመፍታት በመቻሏ ምስጋናዋን አቅርባለች።
ይህ ተግባር “ኢትዮጵያ ታምርት” የሚለውን ሀገራዊ ንቅናቄ ከማጠናከሩ ባሻገር፣ የሴቶችን የፈጠራ አቅም ለህዝብ ጥቅም ማዋል እንደሚቻል ትልቅ ማሳያ ሆኗል።
