የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በ7ተኛው ጠቅላላ ምርጫ የሚወዳደሩ የፓለቲካ ፓርቲዎችና የግል ተወዳዳሪዎች በድምጽ መስጫ ወረቀት ላይ የሚቀመጡበትን ቅደም ተከተል በተመለከተ የእጣ ማውጣት ስነስርዓት በይፋ አስጀምሯል።
በመርሀ ግብሩ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ሜላተ ወርቅ ሀይሉ፥ ቦርዱ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ፍትሀዊ፣ ገለልተኛ እና ስኬታማ እንዲሆን በርካታ የቅድመ ዝግጅት ስራዎችን እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል።
የዚህ አካል የሆነ እና በምርጫው የሚወዳደሩ የፓለቲካ ፓርቲዎችና የግል ተወዳዳሪዎች በድምጽ መስጫ ወረቀት ላይ የሚቀመጡበት ቅደም ተከተልን የሚወስን የእጣ ማውጣት ስነስርዓት በዛሬው እለት በይፋ መጀመሩንም ተናግረዋል።
የእጣ ማውጣት ሂደቱ ግልጽ፣ ፍትሀዊና ተዓማኒ እንዲሆንም የአሰራር ስርዓቶች መዘርጋታቸውም ተገልጿል።
የእጣ ማውጣት ስነስርዓቱ ዛሬን ጨምሮ ለተከታታይ አስር ቀናት የሚቆይ መሆኑንም ዋና ሰብሳቢዋ ገልጸዋል።
የእጣ ማውጣት ሂደቱን የሚመራ፣ የእጣ አወጣጥ መርሀግብሩን የሚከታተል፥ ፓርቲዎች ወይም እጩዎች መገኘታቸውን የሚፈትሽና ቅሬታዎች ሲኖሩ የሚቀበል አካል መዘጋጀቱም በመርሀግብሩ ተመላክቷል።
