ከዓለም ባንክ በተገኘ ድጋፍ 100 የፕላዝማ ፍሪጆች እና አንድ ሺህ ቋሚና ተንቀሳቃሽ ደም መለገሻ አልጋዎች ለክልላዊ ደም ባንኮች መሰጠታቸውን የጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።
ይህ ድጋፍ የደም አቅርቦትን በማሻሻል በተለይ የእናቶችና ህጻናት ሞትን ለመቀነስ የሚያስችል መሆኑን የጤና ሚኒስትር ዶ/ር መቅደስ ዳባ ገልጸዋል።
ዶ/ር መቅደስ የደም ባንክ አገልግሎት ከሌሎች በላይ ጥንቃቄን እንደሚፈልግ አስታውሰው፣ ይህ ድጋፍ አገልግሎቱን በጥራት፣ በተደራሽነትና በፍትሃዊነት ለመስጠት የሚያስችል መሆኑን አክለዋል።
በቀጣይም የደምና ህብረ-ህዋስ አገልግሎትን በሃገር አቀፍ ደረጃ ለማጠናከር እና የክልል ደም ባንኮችን አቅም ለማሻሻል የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ ደምና ህብረ-ህዋስ ባንክ አገልግሎት ዋና ዳይሬተር ዶ/ር አሸናፊ ታዘበው በበኩላቸው፣ ድጋፉ የክልል ደም ባንኮች የግብአት እጥረትን በመቅረፍ ዘላቂ፣ ውጤታማና ደህንነቱ የተጠበቀ የደም አሰባሰብና አቅርቦት ስርአት እንዲኖራቸው አስተዋጾ እንደሚያደርግ ገልጸዋል።
ዳይሬክተሩ አክለውም፣ በድጋፍ የተሰጡት ቁሳቁሶች የደም ግብአትን ለማሻሻል የሚረዱ በመሆናቸው በአግባቡ አገልግሎት ላይ መዋል እንዳለባቸውም አሳስበዋል።
