
ለጅቡቲ ድንበር ተሻጋሪ የመጠጥ ውኃ ፕሮጀክት 12 ነጥብ 2 ሜጋ ዋት ተጨማሪ የኤሌክትሪክ ኃይል መሠረተ ልማት ዝርጋታ መከናወኑን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት አሰታወቀ።
የመጠጥ ውኃ ፕሮጀክቱ ዝርጋታ በሁለት ምዕራፍ ተከፍሎ ሲከናወን ቆይቷል። በመጀመሪያው ምዕራፍ 8 ሜጋዋት ኃይል፣ 36 ኪሜ የመስመር ዝርጋታ እንዲሁም ስምንት ባለ1250 ኬቪኤ ትራንስፎርመር ተከላ ተከናውኗል።
የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴርና ኦንያድ የተሠኘው የጅቡቲ ውኃ ፕሮጀክት ባቀረቡት ተጨማሪ ኃይል ጥያቄ ሁለተኛው ምዕራፍ ሊሰራ ችሏል፡፡
ለውኃ ፕሮጀክቱ 12 ነጥብ 2 ሜጋ ዋት ተጨማሪ ኃይል ከአዲጋላ ሰብስቴሽን 8 ሜጋዋት በ1250 ኬቪኤ ስምንት ትራንስፎርመሮች፤ ቀሪው 4 ነጥብ 2 ሜጋ ዋት በ28 ባለ500 ኪቪኤ፣ 315 ኬቪኤና 400 ኪቪኤ ትራንስፎርመሮች ኃይል እንዲያገኝ ተደርጓል፡፡
በሁለተኛው ምዕራፍ 46 ኪሜ መስመር ዝርጋታና 28 ትራንስፎርመሮች የማስቀመጥ ስራ ተሰርቷል፡፡
በሁለቱም ምዕራፍ በተከናወኑት የመስመር ዝርጋታ የትራንስፎርመር ማስቀመጥ፣የቆጣሪ መግጠም ስራዎች በአጠቃላይ 82 ኪ.ሜ መስመር ዝርጋታ፣ 36 ትራንስፎርመሮች እንዲቀመጡ ተደርጓል፡፡
የአካባቢውን በርሃማ የአየር ፀባይ በመቋቋም ስራውን በስኬታማነት ማጠናቀቅ ተችሏል፡፡ በአሁኑ ወቅት የፕሮጀክቱ የሁለተኛው ምዕራፍ ሥራ ተጠናቆ ርክክብ እየተደረገ መሆኑን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት አስታውቋል።(ኢ ፕ ድ)