ሊዮኔል ሜሲ እና የኢንተር ማያሚ የቡድን አጋሮቹ ያሸነፉትን የሜጀር ሊግ ሶከር ዋንጫ ይዘው ከአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ጋር ተገናኝተዋል። ኢንተር ማያሚ ዋንጫውን በታሪኩ ለመጀመርያ ጊዜ ማሸነፉ ይታወሳል።
የተወሰነ ድርሻው በቀድሞው የእንግሊዝ ብሄራዊ ቡድን ተጫዋች ዴቪድ ቤካም ባለቤትነት የሚተዳደረው ኢንተር ማያሚ ነገ ከዲሲ ዩናይትድ ጋር ከሚያደርገው ጨዋታ በፊት በዋይት ውስ ግብዣ ቀርቦለት ነው በስፍራው የተገኘው፡፡
ፕሬዝዳንት ትራምፕ የኢንተር ማያሚ የቡድን አባላትን ተቀብለው ያነጋገሩ ሲሆን ልጃቸው የሜሲ ትልቅ ደጋፊ መሆኑን ተናግረዋል።
የ8 ጊዜ የባሎን ዶር አሸናፊው ሊዮኔል ሜሲ በጨዋታ ዘመኑ ከኢንተር ማያሚ ጋር 47ኛውን ዋንጫ ማንሳቱን ያስታወሱት ፕሬዝዳንቱ እሱ ወደ የትኛውም የዓለም ክፍል አምርቶ መጫዎት ቢችልም ኢንተር ማያሚን በመምረጡ ደስተኛ መሆናቸውን ገልጸዋል።
የ38 ዓመቱ አርጀንቲናዊ ኮከብ ሊዮኔል ሜሲ ባለፈው ጥቅምት ወር በክለቡ እስከ 2028 ለመቆየት መስማማቱ የሚታወስ ሲሆን የውድድር ዓመቱ ኮከብ ተጫዋች ሽልማትን ለ2ኛ ተከታታይ ጊዜ ማሸነፍ የቻለ የመጀመሪያው ተጫዋችም ነው፡፡
