የሀገሪቱን አስገዳጅ ብሔራዊ እና የገላጭ ጽሁፍ ደረጃ ሳያሟሉ በተጨማሪም ደህንነታቸውና ጥራታቸው ሳይረጋገጥ ገበያ ላይ የዋሉ የለውዝ ቅቤ፣ የምግብ ዘይትና የከረሜላ ምርቶችን ሕብረተሰቡ እንዳይጠቀማቸው የኢትዮጵያ የምግብና መድኃኒት ባለስልጣን አሳስቧል፡፡
ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ለህብረተሰቡ የሚቀርቡ ምግቦች እንደ ለውዝ ቅቤ፣ የምግብ ዘይትና ከረሜላ ምርቶች ላይ ባደረገው የገበያ ቅኝት ቁጥጥር፤ ምርቶቹ የአምራች ድርጅት ሥም ያልተጠቀሰባቸው፣ የአምራች አድራሻ ያልተገለጸ፣ አስገዳጅ የደረጃ ምልክት፣ የምርቱ መለያ ቁጥር የሌላቸው፣ የምርቱ ጥሬ ግብዓት ዝርዝር ያልተገለጸና የመጠቀሚያ እና የማብቂያ ጊዜ የሌላቸው ምርቶችን ማግኘቱን አስታውቋል፡፡
በገበያ ቅኝት ወቅት የተገኙት ምርቶች CES 70 2017 እና የኢትዮጵያ አስገዳጅ ደረጃ ያላሟሉ እና የደረጃ ምልክት ያለጠፉ ስለምርቱ የተለጠፉ ወይም የተፃፉ የምርት ገላጭ ፅሁፍ አስገዳጅ ደረጃ CES 73 2013 ያላሟሉ መሆናቸው መለየት የተቻለ በመሆኑ፤ የምርቶቹን ሕብረተሰቡ እንዳይጠቀማቸውም አሳስቧል፡፡

በገበያ ቅኝት ወቅት የተገኙ ምርቶች ዝርዝር:-
የተለያዩ ለውዝ ቅቤ ምርቶች

- ማዛ የለውዝ ቅቤ
- አያልነህ የለውዝ ቅቤ
- አደይ የለውዝ ቅቤ
- አፊያ የለውዝ ቅቤ
- ስካይ የለውዝ ቅቤ
- ያሚ የለውዝ ቅቤ
የተለያዩ የምግብ ዘይት ምርቶች
- ሙሃ የተጣራ የምግብ ዘይት
- ኤርሚያስ የምግብ ዘይት
- እፎይ የምግብ ዘይት
- እናት የምግብ ዘይት
- ፍትህ የተጣራ የምግብ ዘይት
- ጣራ የተጣራ የምግብ ዘይት
- ዝናሽ ንጹህ የምግብ ዘይት
- አስሊ ንጹህ የምግብ ዘይት
- ንጹህ የምግብ ዘይት
- ዛራ የምግብ ዘይት
- ሞያ የምግብ ዘይት
- እፎይታ ንፁህ የምግብ ዘይት መሆናቸውን ባለሥልጣን መስሪያ ቤቱ አስታውቋል፡፡
በተጨማሪም አስር (10) የተለያዩ ምንም አይነት ገላጭ ጹሁፍ የሌላቸው የከረሜላ ምርቶችን በገበያ ቅኝት ቁጥጥሩ ወቅት ማግኘቱን ባለስልጣኑ አስታውቋል፡፡
