ቀደም ሲል በውጭ ሀገር ይታተም የነበረውን የኢትዮጵያ ፓስፖርት በሀገር ውስጥ ለማምረት የሚያስችል ግዙፍ ፋብሪካ ግንባታ ተጠናቆ በሚቀጥሉት ሁለት እና ሶስት ወራት ውስጥ በይፋ ስራ እንደሚጀምር የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ አስታወቀ።
በቦሌ ለሚ ኢንዱስትሪ ፓርክ የተገነባው ይህ ፋብሪካ “ቶፓን ግራቪቲ ኢትዮጵያ” የሚል ስያሜ የተሰጠው ሲሆን፤ በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ እና በዓለም አቀፉ ቶፓን ግራቪቲ ኩባንያ ትብብር የተመሰረተ ነው። ፕሮጀክቱ በ55 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር ወጪ የተገነባና የሆልዲንጉ የመጀመሪያው አዲስ ኢንቨስትመንት መሆኑ ይታወቃል።
የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ ዋና ስራ አስፈፃሚ ብሩክ ታዬ (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ ይህ ፕሮጀክት የሀገሪቱን ሚስጥራዊ ህትመት ሉዓላዊነት ለማረጋገጥና እስካሁን ይባክን የነበረውን ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ለማዳን ያለመ ነው።
አሁን የማሽነሪ ተከላዉ በሂደት ላይ የሚገኘው ፋብሪካው ስራ ሲጀምር የኢትዮጵያን ማንነት በሚመጥን መልኩ እና የደህንነት መስፈርቶችን ባሟላ ሁኔታ ፓስፖርቶችንና ሌሎች የደህንነት ሰነዶችን ማምረት ይጀምራል።
ከፋብሪካው ግንባታ ጋር ተያይዞ አዲሱ የኢትዮጵያ ኢ-ፓስፖርት (E-Passport) ይፋ መደረጉ ይታወሳል።
በዚህ ግዙፍ የኢንቨስትመንት ስራ ላይ ቶፓን ግራቪቲ የ51 በመቶ ድርሻ ሲኖረው፣ ቀሪው 49 በመቶ ድርሻ ደግሞ በኢትዮጵያ መንግስት (በብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት እና በትምህርት መሳሪያዎች ማምረቻና ማከፋፈያ ድርጅት በኩል) የተያዘ ነው። ፋብሪካው ከፓስፖርት በተጨማሪ ዘመናዊ የመታወቂያ ካርዶች (ID cards) እና የባንክ ካርዶችን በሀገር ውስጥ ለማምረት የሚያስችል ቴክኖሎጂ የታጠቀ ነው።
ፋብሪካው የኢትዮጵያን ፍላጎት ከማሟላት ባለፈ፣ ለጎረቤት ሀገራት እና ለመላው የአፍሪካ ገበያ የፓስፖርት እና የመታወቂያ ህትመት አገልግሎት የመስጠት ሰፊ እቅድ አለው። ይህም ኢትዮጵያ በዘርፉ ያላትን ተወዳዳሪነት የሚያሳድግና ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ የምታገኝበት ሌላኛው መንገድ እንደሚሆን ይጠበቃል።
ይህ ፕሮጀክት በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ አዋጭነታቸው ተጠንቶ ወደ ስራ ካስገባቸው 36 ንቁ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች መካከል አንዱ መሆኑ ተመልክቷል።
( ካፒታል)
