በኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ ውስጥ የሚሳተፉ ባለሙያዎችን ብቃት ለማረጋገጥ ያለመ አዲስ አሰራር ተግባራዊ ሊደረግ መሆኑን የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር አስታውቋል።
የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ይትምጌታ አስራት እንደገለጹት፤ በዘርፉ የሚሳተፉ ባለሙያዎች ከጀማሪ እስከ ከፍተኛ ደረጃ በአግባቡ ሰልጥነውና ህጋዊ የሰርቲፊኬሽን ስርዓት ውስጥ አልፈው ወደ ስራ እንዲሰማሩ ለማድረግ የሚያስችል ስራ እየተሰራ ነው።
ይህ አሰራር ደረጃ በደረጃ ተግባራዊ የሚደረግ ሲሆን፣ ወደፊት ሰርተፊኬት የሌላቸው ባለሙያዎች በየትኛውም ደረጃ በሚገኙ የኮንስትራክሽን ስራዎች ላይ እንዳይሳተፉ የሚያግድና ሙሉ በሙሉ አስገዳጅ እንደሚሆን ሚኒስትር ዴኤታው አስረድተዋል።
ለዚህ አሰራር ውጤታማነት የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር ከስራና ክህሎት ሚኒስቴር ጋር በቅንጅት እየሰራ እንደሚገኝ የተገለጸ ሲሆን፣ ህጉን ሙሉ በሙሉ አስገዳጅ አድርጎ ወደ ትግበራ ከመገባቱ በፊት ምቹ ሁኔታዎችን የመፍጠር ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛል።
ምንም እንኳን ሂደቱ ዓመታትን ሊፈጅ የሚችል ቢሆንም፣ በአሁኑ ወቅት የተግባር እንቅስቃሴው መጀመሩን የኢፕድ ዘገባ አመልክቷል።
