በኦሮሚያ ክልል አርሲ ዞን የጀጁ ወረዳ ነዋሪ የሆነው የአካባቢው ሚሊሻ አባል የህዝብን ደህንነት እንዲጠብቅበት የታጠቀውን መሳሪያ በአስደንጋጭ ሁኔታ የሁለት ሰላማዊ ሰዎች ህይወት እንደቀጠፈበት ነው የተነገረው፡፡
መሃመድ አሚን ከድር የተባለው ተከሳሽ፣ በጀጁ ወረዳ የአላጋ ዱሬ ቀበሌ ሚሊሻ ሲሆን፤ ታህሳስ 13 ቀን 2017 ዓ.ም. ሀሰን ኑሩ የተባለ ተበዳይን የፀጉር ማስተካከል ስራ በሚሰራበት ሄዶ “ለምን ስብሰባ አልወጣህም” በሚል ተኩሶ መግደሉን የአርሲ ዞን አቃቤ ህግ አስታውቋል፡፡
እንደ የዞኑ አቃቤ ህግ ይፋዊ መረጃ፤ ተከሳሹ “ከፀጉር አስተካካይ ባለሙያው ተበዳይ በተጨማሪ በወቅቱ ጸጉር ቤቱ ውስጥ የነበረው ሌላም ግለሰብ በሚሊሻው በተተኮሰ ጥይት ክፉኛ ቆስሎ ሆስፒታል ሲረዳ ቆይቶ ህይወቱ አልፏል” ነው የተባለው፡፡
“ስብሰባ ለምን አልወጣህም ከሚል ንግግር ውጪ ሁለቱ ግለሰቦች መካከል ምንም አይነት ጠብ የለም” የተባለም ሲሆን፤ በግለሰቡ ላይ የጀጁ ወረዳ ፖሊስ መዝገብ ካጣራና ለአርሲ ዞን አቃቤ ህግ ካስተላለፈ በኋላ በግለሰቡ ላይ በተከፈተው ክስ ግለሰቡ ክሱን መከላከል ባለመቻሉ፤ የአርሲ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት መጋቢት 18 ቀን 2017 ዓ.ም. በዋለው ችሎት፣ “የሰው ነፍስን በማጥፋት”፣ ሚሊሻውን በ21 ዓመት ጽኑ እስራት ፈርዶበታል ተብሏል፡፡
በኦሮሚያ ክልል የአካባቢ ታጣቂዎች (ሚሊሻ) በተደጋጋሚ ከህግ ውጪ የሆነ እስርና እንግልት በሰላማዊ ሰዎች ላይ እንደሚፈጽሙና ከህግ አግባብ ውጪ የሆነ ተግባርን የፈጸሙባቸው አጋጣሚዎች መስተዋላቸውን መንግስታዊው የኢትዮጵያ ሰብዐዊ መብቶች ኮሚሽን ከዚህ በፊት በመግለጫ ማሳወቁ አይዘነጋም፡፡
(DW)
