በትግራይ በርካታ ታዳሚ በሚገኝበት በየዓመቱ የሚከበረው የአሸንዳ ባህላዊ በዓል እንደወትሮው በመቀለ ስታዲየም ውስጥ እንደማይከበር ተገለጸ።
የትግራይ ባህል እና ቱሪዝም ቢሮ ዛሬ እንዳስታወቀው ነገ ቅዳሜ ይካሄዳል ተብሎ የነበረው የአሸንዳ በዓል የመክፈቻ ሥነ ሥርዓት በክልሉ ውስጥ እየተጸመ ነው ባለው የድሮን ጥቃት ስጋት ምክንያት መሰረዙን ገልጿል።
ወጣት ሴቶች በባህላዊ አልባሳት እና የልዩ የፀጉር አሠራር ተውበው በጭፈራ ለቀናት የሚያከብሩት በዓል የሆነው አሸናዳ በትግራይ እና በአማራ ክልሎች ውስጥ የሚካሄድ ነው።
በትግራይ የሚካሄደው ሥነ ሥርዓት ባለፉት ዓመታት በርካታ ሕዝብ በሚገኝበት በመቀለ ስታዲየም በደማቅ ሥነ ሥርዓት ሲካሄድ የቆየ ሲሆን፣ በዚህ ዓመት ግን ይህ አከባበር እንደማይኖር ባለሥልጣናት ገልጸዋል።
ባለሥልጣናት የበዓሉ ዝግጅት መሰረዙን ከመግለጻቸው በፊት በክልሉ ውስጥ በሚፈጸም የሴቶች ጥቃት ዙሪያ ተገቢው እርምጃ አልተወሰደም በሚል ጥቁር በመልበስ “ጥቁር አሸንዳ” በሚል ድምጻቸውን ለማሰማት እንቅስቃሴ ማድረግ ጀምረው ነበር።
ይህንንም ተከትሎ የባህል እና ቱሪዝም ቢሮው ከባህላዊው ሥነ ሥርዓት ውጪ ሌሎች እንቅስቃሴዎች መደረግ እንደሌለባቸው አስጠንቅቆ ነበር።
ባለፉት ወራት በፌደራል መንግሥቱ እና በህወሓት መሪዎች መካከል መካሰሶች፣ ግጭቶች እና ጥቃቶች መፈጸማቸውን ተከትሎ በትግራይ ክልል ጦርነት ሊቀሰቀስ ይችላል የሚል ስጋት ተፈጥሯል።
በፌደራል መንግሥቱ የተቋቋመውን ጊዜያዊ መንግሥት አፍርሶ የክልሉን አስተዳደር ህወሓት ከተቆጣጠረ በኋላ በሁለቱ ወገኖች መካከል ያለው ውጥረት እየተካረረ ሄዶ ባለፉት ቀናት የድሮን ጥቃቶች መፈጸማቸው ተዘግቧል
BBC
