በመቀሌ ከተማ የሚገኘው የዴሞክራሲያዊ ስምረት ትግራይ (ስምረት) ፓርቲ ዋና ፅህፈት ቤት፤ በ5 ጣታቂ ኃይሎች መዘረፉን የፓርቲው ኮሙኒኬሽን ዘርፍ ለአሐዱ አስታውቋል።
የትግራይ ዲሞክራሲያዊ ስምረት ፓርቲ የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ዘርፍ ምክትል ኃላፊ አቶ ጣዓመ አረዓዶም፤ ቁጥራቸው አምስት የሚሆኑ ታጣቂዎች 3 የሚሆኑት የልዩ ኃይል መለዮ ለባሾች፣ አንድ የፓሊስ ልብስ እንዲሁም አንድ የሲቪል ልብስ የለበሰ፤ ሁሉም ማስክ በመልበስ ዘረፋ በመፈጸም መሰወራቸውን ለአሐዱ ተናግረዋል።
በአቶ ጌታቸው ረዳ የሚመራው ስምረት ፓርቲ ባለፈው ሳምንት በመቀሌ ከተማ የከፈተው ቢሮ ትናንት ማታ ከምሽቱ 4:45 አካባቢ የፅህፈት ቤቱን ጥበቆች በማስፈራራት ታጣቂዎች ገብተው የተለጣጠፉ ባነሮችን በመገነጣጠል ጥቃት ማድረሳቸውን የገለጹት አቶ ጣዓመ፤ “ነገር ግን በንብረት ላይ የከፋ ውድመት አላደረሱም” ብለዋል።
”ፅህፈት ቤቱ ሁለት ጥበቃዎች የነበሩት ሲሆን፤ አንዱን ይዘውት ሄደዋል” ያሉት የፓርቲው የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ዘርፍ ምክትል ኃላፊው፤ “እስካሁን ድረስ ወደ የፅህፈት ቤቱ ቢሮ ዘልቀን ገብተን ማየት ባንችልንም፤ ነገር ግን ጉዳዩን ፓሊስ እየተከታተለው ነው” በማለት ለአሐዱ አብራርተዋል።
ፓርቲው በመቀሌ ከተማ የሚገኘውን ዋና መስሪያ ቤቱን በመክፈት፤ በመላው ትግራይ አባላትን በመመልመል እና በመመዝገብ ላይ እንደሚገኝም ተናግረዋል፡፡
ፓርቲው በፅህፈት ቤቱ የደረሰውን ጥቃት ተከትሎ ለምርጫ ቦርድ ሪፓርት ማድረጉንም አቶ ጣዓመ ጨምረው ጠቁመዋል።
አክለውም የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር በፓርቲው ፅህፈት ቤት ላይ የተፈጸመውን ሕገወጥ ድርጊት አጣርቶ ዘረፋውን የፈጸሙ አካላትን ለሕግ እንዲያቀርብ እና ሕግን እንዲያስከብር ጠይቀዋል።
ፓርቲው ባሳለፍነው ሳምንት በመቀሌ የከፈተውን ቢሮ አስመልክቶ ሊሰጥ የነበረውን መግለጫ ላልተወሰነ ጊዜ ማራዘሙ የሚታወስ ነው።
(አሐዱ ሬዲዮ)
