የሶሪያው ፕሬዝዳንት አህመድ አል ሻራህ የሽግግር መንግስትን ቅዳሜ እለት ይፋ ያደረጉ ሲሆን 23 ሚኒስትሮችን ሾመዋል። ይህ የካቢኔ ለውጥ ከአሳድ ቤተሰብ አገዛዝ በኃላ የተደረገ ሽግግር እና ሶሪያን ከምዕራባውያን ጋር ያላትን ግንኙነት ለማሻሻል ቁልፍ ምዕራፍ እንደሆነ ተመላክቷል። የሶሪያ አዲሱ የሱኒ አመራር ባለስልጣናት የሀገሪቱን የተለያዩ ጎሳ እና ሀይማኖታዊ ማህበረሰቦችን ያሳተፈ መንግስት እንዲመሰርቱ ከምዕራባውያን እና ከአረብ ሀገራት ጫና ሲደረግባቸው ቆይቷል።
በዚህ ወር በሶሪያ ምዕራባዊ የባህር ጠረፍ በተነሳ ሁከት በመቶዎች የሚቆጠሩ የአላውያን ሲቪሎች ወይም ከስልጣን የተወገዱት መሪ በሽር አል አሳድ የወጡበት አናሳ ጎሳ አባላት መገደላቸውን ተከትሎ ጫናው ጨምሯል። በካቢኔው የትራንስፖርት ሚንስትር ተብለው የተሾሙት ያሩብ በድርን ከአላዊ ጎሳ ሲሆኑ የድሩዝ ማህበረሰብ አባል የሆኑት አማጋድ በድር ደግሞ የግብርና ሚኒስቴርን ይመራሉ። ሂንድ ካባዋት የተባለች ክርስቲያን ሴት በአሳድ አገዛዝ ወቅት የቀድሞ ተቃዋሚዎች አካል የነበረች እና ለሃይማኖቶች መቻቻል እንዲሁም ሴቶችን ለማብቃት ስትሰራ ነበረ በሚል የማህበራዊ ጉዳይ እና የሰራተኛ ሚኒስትር ሆና ተሹማለች።
በታህሳስ ወር ላይ በአሳድ አገዛዝ ላይ መብረቃዊ የተባለው የአማፂያን ጥቃት ከስልጣን ካስወገደ በኋላ ሶሪያ በቀድሞ ጊዜያዊ ካቢኔ ውስጥ የመከላከያ እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ሆነው ሲያገለግሉ የነበሩትን ሙርሃፍ አቡ ከስራን እና አሳድ አል-ሺባኒን በስልጣን ቀጥለዋል። ሻራአ በተጨማሪም ለመጀመሪያ ጊዜ የስፖርት ሚኒስቴር እና የድንገተኛ አደጋ ሚኒስቴር ማቋቋማቸው ተሰምቷል። የነፍስ አድን ቡድን መሪ ራኢድ አል ሳሌህ የድንገተኛ አደጋዎች ሚኒስትር ሆነው ተሹመዋል።
በጥር ወር ሻራአ በጊዜያዊ ፕሬዝዳንትነት ተሰይመዋል። በሶሪያ የተበላሹ የህዝብ ተቋማትን ለመገንባት እና ሀገሪቱን እስከ ምርጫ ድረስ የሚያስተዳድር ሁሉን አቀፍ የሽግግር መንግስት ለመመስረት ቃል ገብተዋል። ይህ ሂደት ግን እስከ አምስት አመታት ድረስ ሊቆይ ይችላል።
@ዳጉ
