
የጥምቀትን በዓልን ምክንያት በማድረግ በታቦተ ህግ ላይ በመሳለቅ በቲክቶክ ያሰራጨ ግለሰብ በ1 ዓመት ከ4 ወር ቀላል እስር እንዲቀጣ መወሰኑን የወላይታ ዞን አረካ ከተማ ፖሊስ ጽ/ቤት አስታውቋል።
ፖሊስ እንደገለፀው ወንጀሉን ከፈፀሙ ግለሰቦች መካከል በቀን 25/05/2017 ዓ.ም በቁጥጥር ስር ውሎ በህግ ጥላ ስር የቆየው ወጣት አቤል አዳፍሬ ነዋሪነቱ በአረካ ከተማ አረዳ ቀበሌ አስተዳደር ውስጥ ሲሆን በማህበራዊ ትስስር ገፅ ለተከታዮቹ ባጋራው የቲክቶክ ቪዲዮ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ክብር የሚነካ የእምነቱ ተከታዮችንም ያስቆጣ ተግባር መፈጸሙ ተገልፆአል።
ፖሊስ የተከሳሹን የምርመራ ሂደቱን ጨርሶ ወደ አቃቤ ህግ በማስተላለፍ አቃቤ ህግ በመሰረተው ክስ ተከሳሹ በተከሰሰበት የወንጀል ህግ ጥፋተኛ በመሆኑ ጉዳዩን ሲመለከት የቆየው ፍርድ ቤት በተከሳሹ ላይ ያስተምራል ያለውን በ 1 አመት ከ 4 ወር ቀላል እሥራት እንዲቀጣ መወሰኑን የዘገበው የከተማዋ ፖሊስ ህዝብ ግንኙነት ነው።
