የፋሽን ኢንዱስትሪውን የወደፊት አቅጣጫ ለመቅረጽ ያለመና በኢትዮጵያ፣ በዚምባብዌ እና በዩናይትድ ኪንግደም ዲዛይነሮች መካከል የሚካሄድ የልምድ ልውውጥ መርሃ ግብር በአዲስ አበባ ተጀምሯል።
(ዝርዝር ዜና): “የፋሽን ረዚደንሲ” (Fashion Residency) የተሰኘውና በብሪቲሽ ካውንስል፣ በፖል ስሚዝ ፋውንዴሽን እና በአጋሮቻቸው የተዘጋጀው ይህ መርሃ ግብር፤ የፈጠራ ኢንዱስትሪውን ዓለም አቀፋዊ ተወዳዳሪነት ለማሳደግ ያለመ ነው።
በመርሃ ግብሩ መክፈቻ ላይ ንግግር ያደረጉት የብሪቲሽ ካውንስል ተወካይ ረሺዳ፤ ስድስት ተማሪ ዲዛይነሮች በለንደን ለስድስት ሳምንታት የሚቆይ ጥልቅ ስልጠና እንደሚያገኙ ገልጸዋል።
ስልጠናው ዲዛይነሮቹ ከዓለም አቀፍ የዘርፉ መሪዎች ጋር እንዲገናኙና የገበያ ትስስር እንዲፈጥሩ ትልቅ ዕድል እንደሚፈጥርም ተመልክቷል።
የኢሳቲስቲክ (isatistic) መስራች ማርቆስ ላ በበኩላቸው፤ የፈጠራ ኢንዱስትሪው ለዓለም ኢኮኖሚ ያለውን ድርሻ አንስተዋል።
እ.ኤ.አ እስከ 2030 ድረስ የዲጂታል እና የባህል ዘርፉ ለሀገር ውስጥ ምርት (GDP) ያለው አስተዋጽኦ 12 በመቶ ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅም በመድረኩ ተገልጿል።
በዝግጅቱ ላይ በተካሄደ የፓናል ውይይት፤ ኢትዮጵያዊቷ ዲዛይነር ሰሎሜ አስፋው በዘርፉ ያለውን የጥሬ ዕቃ አቅርቦት እና የቴክኒክ ስልጠና ውስንነት የገለጸች ሲሆን፤ እንዲህ አይነት መድረኮች ግን አዳዲስ አመለካከቶችን ለማግኘት ወሳኝ መሆናቸውን አስረድታለች።
የዚምባብዌዋ ዲዛይነር ቺዶ በበኩሏ የአፍሪካ ዲዛይነሮች ምርቶቻቸውን በዓለም አቀፍ ደረጃ ለማሳደግ ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸው ጠቁማለች።
ዲዛይነሮቹ በለንደን ቆይታቸው በስቱዲዮ ስሚዝፊልድ በመገኘት በቴክኖሎጂ፣ በንግድ አመራር እና በፈጠራ ክህሎት ዙሪያ ስልጠናዎችን የሚወስዱ ይሆናል።
መርሃ ግብሩ በሀገራቱ መካከል ያለውን የባህልና የፈጠራ ኢኮኖሚ ትስስር ወደ ላቀ ደረጃ ያሸጋግረዋል ተብሎ ይጠበቃል።
