በአዲስ አበባ ከተማ 35 ሺሕ መምህራን በልዩ መታወቂያ ከክፍያ ነፃ የሆነ የትራንስፖርት አገልግሎት እየተሰጣቸው መሆኑን የአንበሳ አውቶቡስ አገልግሎት ድርጅት ገልጿል።
የአዲስ አበባ ከተማ አውቶብስ አገልግሎት ድርጅት ዋና ሥራ አስፈፃሚ አካሉ አሰፉ እንደገለጹት፤ በቀደመው በጀት ለአንድ መምህር በቀን 16 ብር ተመድቦ የትራንስፓርት አገልግሎት እንዲያገኙ እየተደረገ ይገኛል።
ይህ በጀት በአሁኑ ወቅት ወደ አንድ ቦታ ለመድረስ እንኳን የማይበቃ ሊሆን እንደሚችል የገለጹት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፤ ወጪው ከተመደበው በጀት ጋር የማይጣጣም መሆኑን ጠቁመዋል።
መምህራን የሕዝብ አገልጋይና ዜጋን የመገንባትና የማነፅ ሚና ያላቸው በመሆኑ፤ ልዩ መታወቂያው ከክፍያ ነፃ የትራንስፓርት አገልግሎት እንዲያገኙ ለማድረግ ያለመ መሆኑ ገልጸዋል።
በዚህም “መምህራንን ተጠቃሚ ማድረግ ልጆቻቸውን ማስተማር የማይችሉ የሕብረተሰብ ክፍሎችን በተዘዋዋሪ ተጠቃሚ ማድረግ መሆኑ ልብ ሊባል ይገባል” ሲሉ ዋና ሥራ አስፈፃሚው ገልጸዋል።
የከተማ አስተዳደሩም ይሄን ታሳቢ በማድረግ ሥራዎችን እየሠራ መሆኑን ጠቁመዋል።
