የቤት ውስጥ ሠራተኞች ራሳቸውን በሙያ ብቁ የሚያደርጉበት ስልጠና በመስጠትና የሙያ ብቃታቸውን የሚመዝን ፈተና (COC) እንዲወስዱ ለማድረግ እየተሰራበት እንደሚገኝ አንድነት ኢትዮጵያ የቤት ውስጥ ሠራተኞች ማኅበራት ሕብረት አስታውቋል፡፡
የቤት ሠራተኞች በማኅበር ከመደራጀት በዘለለ ስልታዊ የሆነ የሙያ ክህሎታቸውንና ደረጃቸውን ሊመዝኑ የሚችሉ ተቋማቶች በሀገር አቀፍ ደረጃ መኖራቸውን የሕብረቱ ፕሬዝዳንት ሂሩት አበራ ገልጸዋል።
በመሆኑም በሥራና ክህሎት በኩል ተግባራዊ በሚደረገው አሰራር መሠረት ማንኛውም ሰው መሠረታዊ የሆኑ ምዘናዎችን በመውሰድ ራሱን ብቁ ማድረግ የሚችልበት አግባብ በመኖሩ፤ የቤት ሠራተኞችም የትምህርት ደረጃቸው ሳይፈለግ በሙያቸው ብቻ ብቁ መሆናቸውን የሚያረጋግጡበት ምዘና ስለመኖሩ አስታውቀዋል።
በዚህም መሠረት ለሙያው ብቁ መሆናቸውን የሚያረጋግጥ የብቃት ምዘና (COC) እንዲወስዱ ለማድረግ ማኅበሩ እገዛ እያደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
“ከዚህ ጎን ለጎንም ራሳቸውን አብቅተውና የመደራደር አቅማቸውን ጨምረው ከአሠሪዎቻቸው ጋር የሚችሉትን ሙያ በማሳየት ብቁ ከሆኑ በሙያቸውና በምዘናቸው መሠረት የሚቀጠሩበትን መንገድ ለማመቻቸትም እየተሰራበት ይገኛል” ብለዋል።
የሙያ ብቃት ምዘናውን (COC) ማንኛውም ‘በሙያዬ ብቁ ነኝ’ ያለ ሰው ምዘናው በሚሰጥበት ተቋም ውስጥ መፈተን የሚችል ሲሆን ስልጠና የሚያስፈልጋቸው ደግሞ ከአንድ ወር ከግማሽ እስከ 6 ወር በሚደርሱ አጫጭር ስልጠናዎች መሰረት ራሳቸውን ማብቃት እንደሚችሉ ተናግረዋል።
ከዚህ ባሻገርም በኢትዮጵያ ለቤት ሠራተኞች ትምህርትና ስልጠና እንዲሁም ሙሉ ጊዜ ገብተው መሰልጠን የሚፈልጉ የቤት ሠራተኞችን በተመለከተም በዛ ልክ የተዘጋጀ ፖሊሲ ባለመኖሩ ስርዓተ ትምህርቱ ላይ ማስተካከያዎች እንዲደረጉ ከትምህርትና ስልጠና ተቋማት ጋራ እየተሰራበት እንደሚገኝ አስታውቀዋል
