በኢትዮጵያ ዉስጥ 10 ከመቶ የሚሆነዉ ህዝብ ብቻ ነዉ የኤሌክትሪክ ሃይል በመጠቀም ምግብ የሚያበስለዉ ሲል የዉሃ እና ኢነርጂ ሚኒስቴር አስታወቀ ፡፡
ቀሪው የኢትዮጵያ ህዝብ ዛሬም ምግቡን የሚያዘጋጀዉ የማገዶ ቁሶችን በመጠቀም ነዉ ተብሏል ፡፡
ይህ የተገለፀዉ የዉሃ እና ኢነርጂ ሚኒስቴር ከግብርና ሚኒስቴር፣ ከኢትዮጵያ ሶላር ኢነርጅ ልማት እና ከኢትዮጵያ ጀርመን የኢነርጅ ትብብር ጋር በጋራ የሶላር ሃይል ቴክኖሎጂ የምክክር መድረክና ኤግዚቢሽን በተከፈተበት ጊዜ ነዉ፡፡
በመድረኩ ላይ የተገኙት የዉሃ እና ኢነርጅ ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጅነር ሱልጣን ዋሌ ኢትዮጵያ ከፍተኛ ታዳሽ የኤሌክትሪክ ሃይል የማመንጨት አቅም ቢኖራትም መጠቀም አልተቻለም ብለዋል
በዚህም የዉሃ እና ኢነርጅ ሚኒስተር የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ እንደሆነ ገልፀዉ ለአብነት ከአፍሪካ የመጀመሪያ የሆነ ከ 2 መቶ ሜጋ ዋት በላይ የሶላር ሃይል በኢትዮ ሱማሌ ክልል ማመንጨት እንደተቻለ ጠቅሰዋል ፡፡
መንግስት ያለውን ክፍተት ሙሉ ለሙሉ መሸፈን ስለማይችል የሃይል አቅርቦቱን ዘርፍ ለግሉ ባለሀብት ክፍት አድርጎታል ሲሉ ሚኒስትር ዴኤታዉ ተናግረዋል ፡፡
ለግሉ ባለሀብት የተሰጠዉን እድል ኢንቨስተሮች ሊጠቀሙበት እንደሚገባ በምክክር መድረኩ ላይ ተገልጿል፡፡
