በ2017 ዓመት 8ሺ397 ፍቺ ምዝገባ መመዝገቡን የአዲስ አበባ የሲቪል ምዝገባ እና የነዋሪነት አገልግሎት አስታውቋል።
ከተመዘገቡት የፍቺ ምዝገባዎች ውስጥ 3ሺ945 የሚሆኑት በአንድ ዓመት ውስጥ ፍቺው በፍርድ ቤት የተመዘገቡ መሆናቸውን እና 18 ፍቺዎች ደግሞ በሸሪዓ ፍርድ ቤት የተመዘገቡ መሆናቸውን የአገልግሎቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ዮሴፍ ንጉሴ ለብስራት ሬዲዮ ተናግረዋል።
እንዲሁም 29ሺ 806 ጋብቻ ምዝገባ የተደረገ ሲሆን 13ሺ411 በአንድ ዓመት ውስጥ ተከስተው የተመዘገቡ ናቸው። 1ሺ448 የሚሆነው በሸሪዓ ፍርድ ቤት ቅርንጫፍ የተመዘገበ ወቅታዊ ጋብቻ መሆናቸው ተገልጿል።
በዘንድሮው ዓመት 358ሺ 102 ልደት ምዝገባ የተደረገ ሲሆን 91ሺ 597 ህፃናቱ በተወለዱ በ 90 ቀናት የተደረገ ምዝገባ ነው። 14ሺ754 ደግሞ ህፃናቱ በተወለዱ በአንድ ዓመት ውስጥ የተመዘገቡ መሆናቸውን ገልፀዋል።
በሌላ በኩል 290 ጉዲፈቻ ምዝገባ የተደረገ ሲሆን 207 የሚሆኑት በዓመቱ ተከስተው የተመዘገቡ ናቸው። የሞት ምዝገባን በተመለከተ 24 ሺ 193 ሞት የተመዘገበ ሲሆን 11 ሺ 528 የሚሆኑት በአንድ ዓመት ውስጥ ተከስተዋል፡፡
በዓመቱ ከተከሰቱ ኩነቶች ውስጥ 91ሺ597 የሚሆኑትን በ143 ጤና ተቋማት በተከፈቱ ቢሮዎች የተመዘገቡ መሆናቸው እና 86 በመቶ ወቅታዊ ምዝገባ የሚይዝ ነው።
በዓመቱ በወቅቱ የተመዘገበ ኩነት 117 በመቶ በዘገየ የተመዘገበ ኩነት ደግሞ 94 በመቶ ነው።እንዲሁም የግዜ ገደቡ ባለፈበት ደግሞ 82በመቶ ነው።
የተመዘገበው ምዝገባ ከ2016 ዓ.ምጋር ሲነፃፀር ወቅታዊ ልደት 33 በመቶ ጭማሪ፤ ጋብቻ 28 በመቶ ቅናሽ ፣ ወቅታዊ ፍቺ ምዝገባ 50 በመቶ ጭማሪ አሳይቷል ሲሉ አቶ ዮሴፍ ንጉሴ ጨምረው ለብስራት ሬዲዮ ተናግረዋል።
