“ብዙ የውጭ ባንኮች ፈቃድ እየጠየቁ ነው”
የውጭ ባንኮች የኢትዮጵያን የባንክ ዘርፍ መቀላቀላቸው የማይቀር በመሆኑ ለሚጠበቀው ጠንካራ ውድድር፣ የአገር ውስጥ ባንኮች ራሳቸውን ማዘጋጀት እንደሚኖርባቸው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ አሳሰቡ፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ አቶ ማሞ ምሕረቱ አቢሲኒያ ባንክ ከወረቀት ነፃ አገልግሎትን በይፋ ባስጀመረበት ፕሮግራም ላይ፣ የባንክ ዘርፍ እስካሁን ከነበረው በተለየ ውድድርና ፉክክር ይካሄድበታል ብለዋል፡፡
የባንክ ኢንዱስትሪው በሁሉም የአገልግሎት መሥፈርቶች ዘመናዊና ተወዳዳሪ እንዲሆን ግድ የሚልበት፣ ይህንንም የበለጠ አሁናዊ የሚያደርገው ሁለት ምክንያቶች መሆናቸውንም ጠቅሰዋል፡፡
አንደኛው ኅብረተሰቡ ከባንኮች የተሻለ ዘመናዊና ቀልጣፋ አገልግሎት የሚፈልግ በመሆኑ፣ በተለይ ኢንዱስትሪው ለውጭ ባንኮች ክፍት እንዲሆን ከመፈቀዱ ጋር በተያያዘ ጠንከር ያለ ውድድር ስለሚኖር እንደሆነ ማስረዳታቸውን ሪፖርተር በዘገባው ጠቁሟል፡፡
‹‹ብዙ የውጭ ባንኮች ፈቃድ እየጠየቁና ማመልከቻ እያስገቡ ነው፡፡ የውጭ ባንኮች መግባታቸው እርግጥ በመሆኑ፣ ወደድንም ጠላንም በሒደት በጣም ተወዳዳሪና የፉክክር ዘርፍ መሆኑ አይቀርም፤›› ያሉት ገዥው፤ የአገር ውስጥ ባንኮችም ይህንን ታሳቢ ያደረገ ዝግጅት ማድረግ እንዳለባቸው አሳስበዋል ተብሏል፡፡
