ታዋቂው አትሌትና ባለሀብት ሻለቃ ኃይሌ ገብረሥላሴ፣ በደብረ ብርሃን ከተማ በ1.9 ቢሊዮን ብር የገነባውን ሆቴል በይፋ ሥራ ጀምሯል።
ሻለቃ ኃይሌ በምርቃቱ ላይ ባደረገው የምስጋና ንግግር፣ ደብረ ብርሃን የኢንዱስትሪ፣ የሥራ እና የጽናት ከተማ መሆኗን ጠቅሶ፤ ፕሮጀክቱ ተጠናቆ ለአገልግሎት በመብቃቱ የተሰማውን ጥልቅ ደስታ ገልጿል።
አክሎም “እኛ ኢንቨስት ስናደርግ ትልቁ ዓላማችን የሥራ ዕድል መፍጠርና የአገራችንን ገጽታ መገንባት ነው” ብሏል።
ሆቴሉ ሲገነባ የነበሩ ፈተናዎችን በከተማዋ አስተዳደርና በሕዝቡ ድጋፍ ማለፍ እንደተቻለ የገለጸው ሻለቃ ኃይሌ፤ “ ‘አይቻልም’ የሚል ቃል በኢትዮጵያዊያን መዝገበ ቃላት ውስጥ መኖር የለበትም፤ በትጋትና በሥራ ካሰብንበት እንደርሳለን” ሲል የሥራን አስፈላጊነት አጽንኦት ሰጥቷል።
ይህ አዲስ የተመረቀው ሆቴል ለከተማዋ ተጨማሪ ውበትና የቱሪዝም መዳረሻ እንደሚሆን የተገለጸ ሲሆን፣ ማህበረሰቡም ይህን ታላቅ ሀብት እንዲንከባከበው ጥሪ ቀርቧል።
ሻለቃ ኃይሌ ለፕሮጀክቱ መሳካት ድጋፍ ላደረጉ አካላት በሙሉ ምስጋናውን አቅርቧል።
ይህ 11ኛው የኃይሌ ሆቴልና ሪዞርት ፕሮጀክት ለአካባቢው ነዋሪዎች ሰፊ የሥራ ዕድል እንደሚፈጥርና ለከተማዋ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ተገልፁል።
