በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ደቡብ ኦሞ ዞን የዳሰነች ወረዳ ከበኦሞ ወንዝ መሙላት ምክንያት ለተፈናቀሉ ከ79 ሺህ 800 በላይ ዜጎች፣ በተጠለሉበት አካባቢ በቋሚነት መኖር እንዲችሉ የጤና እና የትምህርት መሠረተ ልማትን ጨምሮ ሌሎች መሰረተ ልማቶች መገንባቱ ተገለጸ።
የወረዳው አስተዳዳሪ አቶ ታደለ ሐቴ፤ ከ34 ቀበሌዎች የተፈናቀሉት 79ሺህ 828 ተፈናቃዮች በአሁኑ ወቅት በ12 የመጠለያ ጣቢያዎች ውስጥ እንደሚገኙ ገልጸው፤ በመጠለያ ጣቢያዎቹ ተንቀሳቃሽ የሕክምና አገልግሎት እየተሰጠ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ባለፈው ዓመት የኦሞ ወንዝ ሞልቶ የመኖሪያ አካባቢዎችን በማጥለቅለቁ ምክንያት ነዋሪዎቹ እንደተፈናቀሉ ያስታወሱት የወረዳው አስተዳዳሪ አቶ ታደለ፣ በያዝነው ዓመት ክረምት ተመሳሳይ አደጋ እንዳያጋጥም የቅድመ ጥንቃቄ ሥራዎች እየተሰሩ መሆኑን ጠቁመዋል።
በሌላ በኩል፣ የደቡብ ኦሞ ዞን ቀይ መስቀል ጽሕፈት ቤት ቅርንጫፍ የኦሞ ወንዝ ሞልቶ ጉዳት እንዳያደርስና ወደ ወረዳው ዋና ከተማ ኦሙራቴ እንዳይገባ፣ ከ13 ኪሎ ሜትር በላይ ውሃውን የሚገድብ የካብ ግንባታ ማከናወኑን አስታውቋል።
ይህ የግንባታ ሥራ የክረምቱን የጎርፍ ስጋት ለመቀነስ ያለመ መሆኑ ተገልጿል።
