የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የዲጂታል ባንክ ሥርዓቱን ይበልጥ ዘመናዊና ቀልጣፋ የሚያደርገውን “ስታርፔይ” (StarPay) የተሰኘ የላቀ የዲጂታል መተግበሪያ ዛሬ ጥር 8 ቀን 2018 ዓ.ም በይፋ ወደ ሥራ ማስገባቱን አስታውቋል።
ባንኩ ይህንን አገልግሎት ይፋ ያደረገው ከስታርፔይ ፋይናንሻል ቴክኖሎጂስ (ኤግልላይን ቴክኖሎጂ) ጋር በመተባበር ሲሆን፣ መተግበሪያው ደንበኞች የተለያዩ የባንክ አገልግሎቶችንና ክፍያዎችን በአንድ ቦታ እንዲያገኙ የሚያስችል ነው።
በምርቃት ሥነ-ሥርዓቱ ላይ መልእክት ያስተላለፉት የባንኩ ፕሬዚዳንት ተወካይና የኮርፖሬት አገልግሎቶች ኤክስኪዩቲቭ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ኤፍሬም መኩሪያ እንደገለጹት፣ የዲጂታል ሥርዓት ትግበራ ምርጫ ሳይሆን ግዴታ ወደሆነበት ዘመን መሸጋገራችንን ጠቅሰው የ”ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030″ ራዕይን ለማሳካትም ተቋማት በአጋርነት መሥራት እንዳለባቸው ገልጸዋል።
የኤግልላይን ቴክኖሎጂ መስራችና ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ በርሱፍቃድ ጌታቸው በበኩላቸው፣ ስታርፔይ በተለይ ለነጋዴዎች በርካታ ተግባራትን በአንድ ላይ አጣምሮ በመያዝ ግብይቶችን በእጅጉ የሚያቃልልና የላቀ የክፍያ አማራጭ መሆኑን አስታውቀዋል።
