በኢትዮጵያ በየዓመቱ በካንሰር ከሚጠቁ ከ6 ሺህ እስከ 8 ሺህ ሕፃናት መካከል የሕክምና አገልግሎት ማግኘት የሚችሉት ከ25 በመቶ በታች ብቻ መሆናቸውን የኢትዮጵያ የሕፃናት የደምና ካንሰር ሕክምና ማኅበር አስታወቀ።
የማኅበሩ ፕሬዚዳንት ዶክተር አቤል ኃይሉ በማኅበሩ ምሥረታ መርሐ ግብር ላይ፤ በበሽታው ከሚያዙ ህፃናት 75 በመቶ የሚሆኑት በአቅራቢያቸው የሕክምና ተቋማት ባለመኖራቸው እና በከፍተኛ የገንዘብ እጥረት ምክንያት አስፈላጊውን ሕክምና ሳያገኙ ለሞት እንደሚዳረጉ ተናግረዋል።
የማኅበሩ መመሥረት በዘርፉ ያሉ ባለሙያዎችን እና ባለድርሻ አካላትን በአንድ ጥላ ሥር በማሰባሰብ ለችግሩ የተቀናጀ ሙያዊ ምላሽ ለመስጠት ያለመ መሆኑን የገለጹት ዶክተር አቤል፤ ይህም በሀገሪቱ ለሕፃናት የደም እና የካንሰር ሕክምና ዕድገት አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት መሆኑን አስረድተዋል።
“አንድም ሕፃን በካንሰር መሞት የለበትም” የሚለውን ዓለም አቀፍ መርህ በኢትዮጵያ እውን ለማድረግ፤ መንግሥት እና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች እንዲሁም መላው ማኅበረሰብ ከማኅበሩ ጎን እንዲቆሙ ፕሬዚዳንቱ ጥሪ አቅርበዋል።
ማኅበሩ የሕክምና ተደራሽነትን ለማስፋት፣ የባለሙያዎችን አቅም ለመገንባት እና ወቅታዊ የሕክምና ግብዓቶችን እንዲሁም መድኃኒቶችን በበቂ ሁኔታ ለማቅረብ በትኩረት እንደሚሠራ ተገልጿል።
ይህም በካንሰር የሚጠቁ ሕፃናትን ሕይወት ለመታደግ ወሳኝ መሆኑ በምሥረታው ወቅት ተመላክቷል ሲል የዘገበው ኢፕድ ነው።
