የኢትዮጵያ ግብርና ባለሥልጣን፣ ከአሜሪካ ከብቶችን፣ የአንድ ቀን ጫጩቶችና የሚፈለፈሉ እንቁላሎችን ወደ አገር ውስጥ ለማስገባት የቀረበውን የገበያ ተደራሽነት ጥያቄ ማፅደቁን የአሜሪካ ግብርና መሥሪያ ቤት አስታወቀ።
ይህ ታሪካዊ የተባለለት የገበያ ፈቃድ የተረጋገጠው ታህሳስ 7 ቀን 2018 ዓ.ም ሲሆን፣ ይህም በሁለቱ አገራት መካከል ለዓመታት ሲካሄድ የቆየው የቴክኒክ ድርድር መጠናቀቁን የሚያመለክት መሆኑ ተጠቁሟል።
ባለፉት ጥቂት ዓመታት የአሜሪካ የእንስሳትና ዕፅዋት ጤና ምርመራ አገልግሎት፣ ከኢትዮጵያ ግብርና ሚኒስቴርና በቅርቡ ደግሞ ከኢትዮጵያ ግብርና ባለስልጣን ጋር በቅርበት ሲሰራ መቆየቱ ተገልጿል።
የዚህ ትብብር ዋና ዓላማ ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ የእንስሳት ጤና የምስክር ወረቀቶችን ማዘጋጀት ሲሆን፣ አሁን ላይ ሰነዶቹ በመጽደቃቸው በህይወት ያሉ እንስሳትን ከአሜሪካ ወደ ኢትዮጵያ ለማጓጓዝ የሚያስችል ሙሉ ህጋዊ መሠረት ተጥሏል ሲል ካፒታል ዘግቧል።
ቀደም ሲል አሜሪካ የበሬ ዘር እና ፅንስ ወደ ኢትዮጵያ ለመላክ ፈቃድ አግኝታ የነበረ ቢሆንም፣ አሁን የተገኘው ፈቃድ ግን በህይወት ያሉ እንስሳትን በቀጥታ ለማስገባት የሚያስችል በመሆኑ ለዘርፉ ትልቅ እመርታ ተደርጎ መወሰዱን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
ከፍተኛ ምርት የሚሰጡ የአሜሪካ ዝርያዎች ወደ አገር ውስጥ መግባታቸው፣ አርሶ አደሮችና ባለሀብቶች በትንሽ እንስሳት ቁጥር ከፍተኛ የወተትና የስጋ ምርት እንዲያገኙ ያስችላቸዋል ተብሏል።
በተለይም በዶሮ እርባታ ዘርፍ ጥራት ያላቸው የአንድ ቀን ጫጩቶችና የሚፈለፈሉ እንቁላሎች እጥረት ለዘርፉ እድገት ትልቅ ማነቆ ሆኖ መቆየቱ ይታወቃል።
