የኢራኑ ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ መገደላቸውን የኢራን መንግሥት አረጋግጦ 40 የሐዘን ቀናት አወጀ።
መሪው እስራኤል እና አሜሪካ ቅዳሜ ዕለት ቴህራን ውስጥ በፈጸሙት ጥቃት መገደላቸውን የአገሪቱ የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን አረጋገጡ።
ከኢራን ብሔራዊ የደኅነንት ጠቅላይ ምክር ቤት ወጥቶ በአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን በተነበበው መግለጫ ላይ እንደተገለጸው አያቶላህ ኻሜኒ የተገደሉት ቅዳሜ ጠዋት ጽህፈት ቤታቸው ላይ በተፈጸመው ጥቃት ነው።
የጠቅላይ መሪውን ሞት ተከትሎ በመላው አገሪቱ 40 የሐዘን ቀናት የታወጀ ሲሆን፣ የባለሙያዎች እና የሃይማኖት መሪዎች ምክር ቤት የሆነው የአመራር ጉባዔ በአስቸኳይ የተገደሉትን መሪ የሚተካ ሰው ይሾማል ተብሎ ይጠበቃል።
የአገሪቱ ፕሬዝዳንት እና ሌሎች ሁለት ከፍተኛ ባለሥልጣናት በቀጣይ የሚደረገውን የመሪ ሽግግር እንደሚመሩ ተገልጿል።
በቅዳሜ ዕለቱ ጥቃት ከአያቶላህ ኻሜኒ በተጨማሪ ከ200 በላይ ሰዎች መገደላቸውን ቀይ ጨረቃ እና ሌሎችም ምንጮች ያስታወቁ ሲሆን፣ ከእነዚህም መካከል 40 የሚሆኑት የኢራን መንግሥት ባለሥልጣናት እንደሆኑ እየተነገረ ነው።
በጥቃቱ የኻሜኒ ሴት ልጅ፣ ባሏ እና የልጅ ልጃቸው መገደላቻውን ከኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ጋር ቅርብት ያላቸው መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።
