የአዲስ አበባ ገቢዎች ቢሮ የ2017 የግብር ዘመን አዲስ የአወሳሰን ስርዓት ከሐምሌ 1 ቀን 2017 ዓ.ም. ጀምሮ ተግባራዊ እንዲሆን ማድረጉን አስታወቀ። ይህ አዲስ መመሪያ የመኖሪያ ቤት አከራዮችን፣ የሙያ አገልግሎት ሰጪዎችን፣ እንዲሁም አንዳንድ የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎችን ይመለከታል።
የንግድ ስራ ያልሆነ ገቢ ያላቸው የመኖሪያ ቤት አከራዮች እና የንግድ ፍቃድ ሳይኖራቸው በሙያ ፍቃድ ብቻ አገልግሎት የሚሰጡ ግለሰቦች (እንደ ጠበቆችና ኢንሹራንስ ወኪሎች ያሉ) ከጠቅላላ ገቢያቸው 35 በመቶው እንደ ወጪ የሚቀነስ ሲሆን፣ ቀሪው 65 በመቶው ብቻ ግብር የሚከፈልበት ገቢ ይሆናል።
ይህ አሰራር የሂሳብ መዝገብ ማቅረብ ግዴታ ሳይኖርባቸው በግምት ገቢያቸው የሚሰላላቸውን ግብር ከፋዮች ጫና ለመቀነስ እና የግብር አሰባሰቡን ፍትሃዊ ለማድረግ ያለመ መሆኑን ካፒታል ከመመሪያው ለመረዳት ችሏል።
ከዚህ በተጨማሪ በህግ ደረሰኝ የመጠቀም ግዴታ የሌለባቸው የከተማ ውስጥ የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎች እንዲሁም በግል ኮድ 02 እና በንግድ ኮድ 03 የተመዘገቡ ተሽከርካሪ የኪራይ አገልግሎት ሰጪዎች ላይም አዲሱ መመሪያ ተፈፃሚ ይሆናል። ለእነዚህ ዘርፎች ግብሩ የሚሰላው በሰንጠረዥ “ሐ” መሰረት መሆኑን ተገልጿል።
ከእነዚህ ዘርፎች ውጭ የሆኑ እና የሂሳብ መግለጫ የማቅረብ ግዴታቸውን ያልተወጡ ግብር ከፋዮች ግን ግብር ለመሸሽ በሚደረግ ተግባር እንደሚወገዱ ቢሮው አስጠንቅቋል። በዚህም መሰረት፣ የታክስ ጉዳቱ 40 በመቶ እና የታክሱ እጥፍ ቅጣት ሳይነሳ ገቢው እንደሚሰበሰብ ተገልጿል።
CapitalNews
