ኢትዮጵያ ባለፉት ስምንት ወራት ብቻ ከአበባ ምርት ዘርፍ 366 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር ገቢ ማግኘቷን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ። ይህ የተነገረው 9ኛው የሆርቲፍሎራ ኤክስፖ በግብርና ሚኒስትሩ ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) ንግግር በተጀመረበት ወቅት ነው፡፡
ሚኒስትሩ እንደገለጹት፣ የሆርቲካልቸር ዘርፍ በአሁኑ ጊዜ በሀገሪቱ ውስጥ ከሚገኙት ከፍተኛ ሶስት የውጭ ምንዛሬ ከሚያስገኙ ዘርፎች መካከል አንዱ ሆኗል። በተለይም ዘርፉ ለወጣቶች በርካታ የስራ እድሎችን በመፍጠር፣ ከ80 በመቶ በላይ የሚሆኑት ሰራተኞች ሴቶች መሆናቸው ተገልጿል።
በተጨማሪም፣ ኢንዱስትሪው በአገሪቱ በተለያዩ አካባቢዎች የአነስተኛ፣ መካከለኛ እና ትላልቅ ኢንተርፕራይዞች እንዲስፋፉ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል።
ይሁን እንጂ፣ ሚኒስትሩ ከፍራፍሬ፣ አትክልትና ቅጠላ ቅጠሎች የኤክስፖርት እድሎች በአግባቡ ጥቅም ላይ አለመዋላቸውን ጠቁመዋል። የአለም የአኗኗር ዘይቤ ወደ ፍራፍሬ እና አትክልት ፍጆታ እየተቀየረ መሆኑን በመገንዘብ መንግስት ለግል ዘርፍ ተሳታፊዎች የተሻለ ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር የፖሊሲ እና የዘርፍ ማሻሻያዎችን እያደረገ ነው ብለዋል።
ለሶስት ቀናት በሚቆየዉ በሆርቲፍሎራ ኤክስፖ ላይ የአካባቢ ጥሩ አስተዳደር ልማት፣ የአካባቢ ጥሩ የግብርና ልምዶችና አግሮ-ሎጂስቲክስ አስፈላጊነት፣ የአውሮፓ ህብረት አዳዲስ ደንቦች ጨምሮ በሌሎች ወሳኝ ጉዳዮች ላይ ዉይይት እንደሚደረግ ይጠበቃል ።
የኢትዮጵያ ሆርቲካልቸር አምራች ላኪዎች ማህበር “ሆርቲካልቸር ለዘላቂ ኢትዮጵያ” በሚል መሪ ቃል የሚያዘጋጀው የሆልቲ ፍሎራ ኤክስፖ ለ9ኛ ጊዜ በዛሬው እለት ሚኒስትሮች ፣ አምራቾች፣ አምባሳደርች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት በሚሊኒየም አደራሽ ተከፍቷል::
CapitalNews
