በ2017 በጀት ዓመት ስምንት ወራት ወደ ተለያዩ ሀገራት ከተላከ ቡና ከ1.2 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱን የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለሥልጣን አስታውቋል።
በበጀት ዓመቱ ከቡና ወጪ ንግድ 2 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር ገቢ ለማግኘት ታቅዷል። በስምንት ወራት 169ሺህ ቶን ቡና በመላክ 916 ነጥብ 48 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ለማግኘት እቅድ ተይዞ ነበር።
ከታቀደው በላይ 257ሺህ ቶን ቡና በመላክ 1.226 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር ገቢ መገኘቱን ባለሥልጣኑ አስታውቋል። በተገኘው ገቢ 134 በመቶ እንዲኹም በተላከው የቡና መጠን 152 በመቶ የእቅድ አፈጻጸም በማስመዝገብ የላቀ ውጤት መገኘቱን አመልክቷል።
የኢትዮጵያ የቡና ምርታማነት በከፍተኛ ኹኔታ እያደገ መኾኑንም በመረጃው ላይ ተገልጿል። ኢትዮጵያ በተያዘው በጀት ዓመት 400ሺህ ቶን ቡና በመላክ 2 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር ገቢ ለማግኘት ማቀዷን ከባለሥልጣኑ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
