ኢትዮጵያ ከመጋቢት 18 እስከ 19 በብራዚል በተካሄደው በመካከለኛው ምስራቅ እና ሰሜን አፍሪካ የብሪክስ ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች እና ልዩ መልዕክቶች ስብሰባ ላይ ተሳትፋለች፡፡ በብራዚል የኢትዮጵያ አምባሳደር ልዑልሰገድ ታደሰ በስብሰባው ላይ ባደረጉት ንግግር በመካከለኛው ምስራቅ እና ሰሜን አፍሪካ ቀጣና ያሉ ግጭቶች እና ሰብዓዊ ቀውሶች ኢትዮጵያን እንደሚያሳስቧት ገልፀዋል።
ኢትዮጵያ ለሱዳን ግጭት ዲፕሎማሲያዊ መፍትሄ ለማምጣት ጥረት እያደረገች እንደሆነ ያከሉት አምባሳደሩ፤ አቅም ያላቸው የብሪክስ አባል ሀገራት ለሱዳን ሰብዓዊ ቀውስ ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።
ኢትዮጵያ በቀይ ባሕር እና በሕንድ ውቅያኖስ ዳርቻ የምትገኝ ከፍተኛ የሕዝብ ቁጥር ያላት ሀገር መሆኗንም አስታውሰው፤ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በቀይ ባሕር እና ሕንድ ውቅያኖስ ላይ አካታች ዓለም አቀፋዊ ትብብርን ቢያበረታታ ተጠቃሚ ይሆናል ብለዋል።
ስብሰባው ባወጣው የጋራ መግለጫ በመካከለኛው ምሥራቅ እና በሰሜን አፍሪካ የቀጠሉ ግጭቶች አሳሳቢ እንደሆኑ አበክሮ መግለፁን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
