ኦክሎክ ሞተርስ 24 ሰአት የሚሰራ የተሽከርካሪ ማሳያ (Show Room) እና የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የጥገና ማዕከል አስመርቋል
በመርሀግብሩ የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባ እና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ጃንጥራር አባይና ሎሎች ጥሪ የተደረገላቸው አካላት የተገኙ ሲሆን ድርጅቱ የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ሚኒስቴር ከኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ሽያጭ ጋር በተያያዘ ባወጣው መመሪያ መሠረት ለደንበኞቹ የተቀላጠፈ አገልግሎት ለመስጠት በሚያስችል ሁኔታ ምቹ በሆነ ሥፍራ የመኪና ማሣያ (Show Room) እና የተሽከርካሪ ጥገና ማዕከል በባለሙያዎችና በማሽነሪዎች ማደራጀቱ ተጠቁሟል፡፡
በቀጣይ በዚሁ ማዕከል ሃያ አራት ሰዓት የተለያዩ የነዳጅና የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን የጥገና እና የፍተሻ አገልግሎት ለመስጠት መዘጋጀቱም ተነግሯል፡፡
ኦክሎክ ሞተርስ በሀገራችን በኤሌክትሮኒክስ ክፍያ የሚሰሩ ዘመናዊ የአቫንዛ ታክሲዎችን ሥራ በማስጀመር እንዲሁም በቱሪዝም ትራንስፖርት ዘርፍ ላይ የሚስተዋሉ የትራንስፖርት አገልግሎት ጥራት ችግሮችን ለመቅረፍ ባሉት ሁለት የተሽከርካሪ መገጣጠሚያ ፋብሪካዎቹ የውሊንግ ተሽከርካሪዎችን እየገጣጠመ ለማህበራትና ለግለሰቦች ማስረከቡ ተገልጿል፡፡
ከዚሁ ጋር በተያያዘ ድርጅቱ በጥገና ማዕከሉ ገጣጥሞ ላስረከባቸው ሁሉም ዓይነት ተሽከርካሪዎች የመለዋወጫ ክምችት ያለው ሲሆን መንግስት በቅርቡ ከኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ጋር በተያያዘ ያወጣውን መመሪያ ተከትሎ ድርጅቱ ሰባት ዓይነት የውሊንግ ኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ገጣጥሞ ለሽያጭ ዝግጁ አድርጓል ተብሏል፡፡
እነዚህ ተሽከርካሪዎች ለግልና ለትራንስፖርት አገልግሎት ሊውሉ የሚችሉ ከአምስት አስከ አሥራ አራት ተሳፋሪ መጫን የሚችሉ ተሽከርካሪዎች ናቸው፡፡
ኦክሎክ ሞተርስ ከሃያ ዓመት በፊት ምስረታውን አድርጎ በተለያዩ የንግድ ሥራ ዘርፎች ላይ ተሰማርቶ እየሰራ የሚገኝ ሀገር በቀል የንግድ ድርጅት ነው፡፡
