እንደ ድርጅቱ ዓለም አቀፍ እርዳታ መቀነሱ ለብዙ አሥርት ዓመታት የህጻናት ሞትን ለመከላከል በተደረገው ጥረት የተገኘውን ውጤት የሚገታ እና ሁኔታውንም እስከመቀልበስ የሚያደርስ ነው ። የተባበሩት መንግስታት የህጻናት መርጃ ድርጅት UNICEF በዓመታዊ ዘገባው የእርዳታ ገንዘብ ቅነሳ መዘዝ በተለይ አሁንም ከሰሀራ በታች በሚገኙ ሀገራት ከፍተኛ የሆነው የህጻናት ሞት እንዲባባስ ምክንያት መሆኑ እንደማይቀር አስጠንቅቋል።
የድርጅቱ የጤና ጉዳዮች ተባባሪ ሃላፊ ፋውዝያ ሻፊክ እንደሚሉት በጎርጎሮሳዊው በ2023 ዓም እድሜያቸው ከአምስት ዓመት በታች የሆነ ህጽናት ሞት እየቀነሰ መሄዱ የተመዘገበበት ዓመት ነበር። ያም ሆኖ በዓመቱ 4.8 ሚሊዮን ህጻናት ሞተዋል። ይህም ከፍተኛ ቁጥር መሆኑን ሳይጠቅሱ አላለፉም።
ከዚህ ሌላ የእርዳታ ቅነሳው የጤና ሰራተኞች እጥረት ፣የክሊኒኮች መዘጋትን የክትባት መርሀግብር መዛባትን እና ወባን የመሳሰሉ በሽታዎችን ለመከላከል የሚያስፈልጉ መሰረታዊ አቅርቦቶችን እጦትም አስከትሏል። ተባባሪ ሃላፊዋ እንዳሉት በዚህ ረገድ የወባ ተጠቂዎች ቁጥር እየጨመረ የመጣባትን ኢትዮጵያን እንደምሳሌ አንስተዋል። ሀገሪቱ የምርመራ አገልግሎት ፣ ወባን ለመከላከል የሚረጩ መድኃኒቶች ፣እና የአጎበሮች እንዲሁም ለበሽታው መከላከያ የሚካሄዱ ዘመቻዎችን ለሚደግፍ እርዳታ እጥረት ተጋፍጣለች።
