129ኛው የአድዋ ድል መታሰቢያ በዓል የምርት ገበያው አመራሮች፣ ሠራተኞችና ተገበያዮች በተገኙበት የካቲት 21 ቀን 2017 ዓ.ም በምርት ገበያው ዋና መሥሪያ ቤት ተከበሯል፡፡
በክብረ በዓሉ ላይ አቶ መርጊያ ባይሣ የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ዋና ሥራ አስፈፃሚ መልዕክት ያስተላለፉ ሲኾን አባቶቻችን በከፈሉት መስዋዕትነት ነፃነትና ክብር ያላት ሀገር በመረከባችን ዕድለኞች ነን፣ ለዚህ ክብር ያበቁን ጀግኖች አባቶቻችን ክብርና ምስጋና ይገባቸዋል ብለዋል፡፡
አድዋ የጥቁር ህዝቦች የነጻነትና የጀግንነት መገለጫ ነው፡፡ የዚህ ዘመን ትውልድ የአባቶቻችንን አደራ በመረከብና ዘመኑ የሚጠይቀውን ጀግንነት በመፈፀም ሀገራችን ወደ ብልፅግና ለመሻገር የሚደርገውን ጥረት በባለቤትነት የማሳካት አደራ አለበት ብለዋል፡፡
ዋና ሥራ አስፈጻሚው አክለው የምርት ገበያው አመራሮች፣ ሠራተኞችና ተገበያዮች በተሰማሩበት የሥራ ዘርፍ በታማኝነትና በትጋት በማገልገል የጥቁር ህዝቦች የነጻነት ተምሳሌት የሆነቸውን ሀገራችን ኢትዮጵያን የብልፅግና ተምሳሌት ለማድረግ የተጀመረውን ጥረት ለማሳካት ከምን ጊዜውም በላይ ርብርብ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
ለክብረ በዓሉን የተዘጋጀውን የመወያያ ሰነድ አቶ ዳዊት ሙራ የኢትዮጵያ ምርት ገበያ የኮርፖሬት ኮምዩኒኬሽን ሥራ አስኪያጅ አቅርበገው ውይይት ተደርጎበታል፡፡
