አገልግሎቱ በሩብ ዓመቱ ይዞት ከነበረዉ ዕቅድ በታች መፈጸሙን ነዉ የሰማነዉ፡፡
የአገልግሎቱ የህዝብ ግንኙነትና ኮሚኒኬሽን ስራ አስፈፃሚ ተወካይ አቶ ነጋ ደምሴ ከጣቢያችን ጋር በነበራቸዉ ቆይታ፤በሩብ ዓመቱ በሀገር አቀፍ ደረጃ ለመሰብሰብ ታቅዶ የነበረዉ 1መቶ 83 ሺህ ዩኒት ደም እንደነበር አንስተዋል፡፡
በአጠቃላይ የተሰበሰበዉ ግን ከታቀደዉ ዝቅ ያለ መሆኑን የገለጹት ስራ አስፈጻሚዉ፤ 1መቶ 59 ሺ 1መቶ 60 ዩኒት ደም መሰብሰብ መቻሉን ነግረዉናል፡፡
በመዲናዋ ብቻ ለመሰብሰብ ታቅዶ የነበረዉ 42 ሺ 8መቶ ዩኒት ደም እንደነበር አንስተዉ፤ 37 ሺ 6መቶ26 ዩኒት ደም መሰብሰብ መቻሉን ገልጸዋል፡፡
አገራችን ያለችበት የፀጥታ ሁኔታ ደም ለመሰብሰብ ችግር አልሆነብንም ያሉት አቶ ነጋ፤ አሁን አንደ ችግር እየተነሳ ያለዉ የአለም ጤና ድርጅት የሚያስቀምጠዉ መስፈርት መሆኑን አንስተዋል፡፡
ከህዝብ ብዛት አንፃር እንደ አገር 1 በመቶ የሚሆነዉ ደም መለገስ አለበት ሲል የዓለም ጤና ድርጅት ቢገልጽም፤ ኢትዮጵያ አሁን እዛ ደረጃ ላይ መድረስ አልቻለችም ብለዋል፡፡
ደም ለመለገስ በማህበረሰቡ ዘንድ የግንዛቤ ዕጥረት መኖሩን እንዲሁም የሀይማኖት ጉዳይ ምክንያት ሆኖ በተደጋጋሚ እንደሚነሳ ገልጸዉ፤ ይሄን ለመቅረፍ ከሀይማኖት አባቶች ጋር በየጊዜዉ እየተወያዩ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
