የዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ የቦርድ አባላት የእስራኤል ወታደራዊ ጥቃት በኢራን የኒውክሌር ተቋማት ላይ የሚያስከትለውን አደጋ ለመወያየት ዛሬ በኤጀንሲው ዋና መሥሪያ ቤት አስቸኳይ ስብሰባ ያደርጋሉ።
ስብሰባው የተጠራው በኢራን ሲሆን የሩሲያ፣ቻይና እና ቬንዙዌላን ድጋፍ አግኝቷል።
ኢራን መጀመሪያ ላይ በሳምንቱ መጨረሻ የእስራኤልን ጥቃት የሚያወግዝ የውሳኔ ሃሳብ ማቅረብ ፈልጋ ነበር።
ይሁንና ቢቢሲ ያነጋገራቸው የዲፕሎማቲክ ምንጮች እንደገለፁት የውሳኔ ሃሳቡ የብዙሃኑን ድጋፍ ያስገኛል ተብሎ አይታሰብም።
በዚህም ምክንያት ኢራን አሁንም የእስራኤልን ድርጊት ማውገዝን ያካተተ አጠቃላይ መግለጫ ለማቅረብ ተዘጋጅታለች።
ይህ አስቸኳይ ስብሰባ የተጠራው በኢራን እና በእስራኤል መካከል እየተካሄደ ያለው የሚሳዔል ልውውጥ መካከል እስራኤል በናታንዝ እና ፎርዶው የሚገኙ የኢራን የኒውክሌር ቦታዎች ላይ ያነጣጠረ ጥቃት መሰንዘሯን ተከትሎ ነው።
የኒውክሌርን ስጋት ለመፍታት ወታደራዊ እርምጃ በኤጀንሲው አባል አገራት ስምምነት መሠረት ተቀባይነት ያለው መንገድ ሆኖ አያውቅም።
ኢራን ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ እና የኤጀንሲው የቦርድ አባላት ጥቃቱን ማውገዝ እንዳለባቸው አጥብቃ ትናገራለች።
ሆኖም አሁን ካለው የፖለቲካ ሁኔታ አንፃር እንዲህ ዓይነቱ ውግዘት የሚጠበቅ አይደለም።
በተጨማሪም ይህ ስብሰባ በሁለቱ ኃያላን አገራት መካከል በአፋጣኝ የተኩስ ማቆም እንዲደረግ መንገድን ስለ መክፈት አለመክፈቱ ግልፅ አይደለም።
ሁለቱ አገራት አንዳቸው በሌላኛቸው ላይ ጠንካራ የአጸፋ ጥቃት መስጠታቸውን ቀጥለዋል።
