የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር መሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ የልማት ተነሺ ፋይሎችን በማዘግየቱ እንዳሳሰባቸው የገለፁ ነዋሪዎች የፋይሎቹ ባለቤቶችና ህጋዊ ወኪሎች ምላሽ ማግኘት እንዳልቻሉ ተናግረዋል።
ለድሬዳዋ ከንቲባ ቅሬታቸውን ለማቅረብ ቢሞክሩም ፈጽሞ እንደማይቻል እና የከንቲባው የአገልግሎት ቀን በግልጽ እንደማይታወቅም ጭምር ለመሠረት ሚድያ አስረድተዋል።
“የድሬዳዋ አስተዳደር መሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ሲያስተናግዳቸው የነበረውን የልማት ተነሺ ፋይሎች ለሁለት ዓመታት በማገድ የአስተዳደሩ የካቢኔ አባላት ቤተሰቦች እና ዘመዶች ግን እየተስተናገዱ ነው” በማለት ተናግረዋል።
“ህጋዊ ወኪል እና የፋይሉ ባለቤቶች ሲጠይቁ ግን ታግዷል ይባላሉ፣ ከንቲባው ነው ያገደው ምንም ማድረግ አንችልም እያሉ መልስ ይሰጣሉ” ብለው ለሚድያችን ቃላቸውን የሰጡ እነዚህ በርከት ያሉ ነዋሪዎች አብዛኛው የልማት ተነሺ፣ ህጋዊ የፋይሉ ባለቤቶችና ወኪሎች አቤቱታ የሚያቀርቡበት ቦታ አጥተው እየተንከራተቱ እንዳሉ ተናግረዋል።
“ለድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ከድር ጁሀር አቤቱታ ለማቅረብ ብንሞክርም በተደጋጋሚ ፈጽሞ ማግኘት እንደማይቻልና በግልጽ የተቀመጠ የአገልግሎት ቀን ከንቲባው እንደሌለው ተነግሮናል” ብለው ለመሠረት ሚድያ የተናገሩት ነዋሪዎች ከንቲባው ባጋጣሚ ቢሮ ቢገኙ እና ለማናገር ቢሞክሩ እንኳን የድሬዳዋ ከተማ አድማ በታኝ ፖሊሶች ተገልጋዮችን እየደበደቡ እንደሚመልሱ ጠቁመዋል።
“ከንቲባውን ሊያገኙ የሚችሉት ሰዎች ጥቂት ባለሀብቶች እና የገጽታ ግንባታ ላይ ያሉ የሶሻል ሚዲያና የሚዲያ ሰዎች ብቻ ናቸው” ብለዋል።
በርካታ መፈታት ያለባቸው ጉዳዮች እንዳሉ የሚጠቅሱት ነዋሪዎቹ የልማት ተነሺዎች የምትክ መሬት ጉዳይ አስቸኳይ መፍትሄ እንደሚፈልግ እንዲሁም በአጠቃላይ የድሬዳዋ ህብረተሰብ የተለያዩ ቅሬታውን ማቅረብ ስላልቻለ የከንቲባው የአገልግሎት ቀን በግልጽ ማወቅ እንፈልጋለን በማለት ተናግረዋል።
በዚህ ዙርያ ከንቲባ ከድርን ለማነጋገር በተደጋጋሚ ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም፣ ምላሽ ከሰጡን ይዘን እንመለሳለን።
@MeseretMedia
