የግብጹ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ባደር አብደላቲ፣ ግብጽ በናይል ወንዝ አጠቃቀም ላይ “ሊታለፉ የማይችሉ ቀይ መስመሮች አሏት” በማለት ለአንድ የአገራቸው ቴሌቪዥን ጣቢያ በሠጡት ቃል የናይል ተፋሰስ አገራትን አስጠነቀቁ።
አብደላቲ፣ አንዱ የግብጽ ቀይ መስመር ከድርሻዋ “አንድም ጠብታ ውሃ” አለማስወሰድ መኾኑን ጠቅሠዋል። ግብጽ ቀይ መስመሮቿን የማለፍ ሙከራ ካየች ፈጣን ርምጃ ትወስዳለች በማለት አብደላቲ አስጠንቅቀዋል።
አብደላቲ፣ በናይል ወንዝ ላይ ከእንግዲህ ከግብጽ እውቅና ውጭ ማንም የተፋሰሱ አገር ግድብ እንዳይገነባ ጭምር አሳስበዋል። በተለይ የኢትዮጵያው ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ከተመረቀ ወዲህ፣ የግብጽ ባለሥልጣናት በግድቡ አስተዳደር እና ባጠቃላይ በወንዙ ውሃ አጠቃቀም ላይ ያነጣጠሩ ተከታታይ ማስጠንቀቂያዎችን በማውጣት ላይ ናቸው ስትል ዋዜማ ዘግባለች፡፡
