በኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ታሪክ ውስጥ ደማቅ አሻራ ያሳረፉትን የቀድሞውን ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጸሐፌ ትዕዛዝ አክሊሉ ሀብተ-ወልድን የሕይወት ጉዞ የሚዘክር አዲስ መጽሐፍ ተመረቀ።
መጽሐፉ የአክሊሉ ሀብተ ወልድን የፖለቲካ ሕይወት ብቻ ሳይሆን ሰብአዊ ባህሪያቸውን፣ ስሜቶቻቸውን እና የልጅነት ትዝታዎቻቸውን በታሪካዊ ልብ-ወለድ (Biographical Fiction) መልክ የሚያቀርብ ነው።
መጽሐፉ የታሪክ መዛግብት ላይ ከሚገኙት ደረቅ መረጃዎች ወጣ ባለ መልኩ፣ የአክሊሉን ሕይወት “ከመወለድ እስከ ገነት” በሚል እይታ ይተርካል። ይህም የአንባቢን ልብ በሚነካ እና ስሜትን በሚያጋራ የፈጠራ ስልት የቀረበ ነው።
መጽሐፉ በዶክተር ሰላማዊት ታደሰ የተዘጋጀ ሲሆን፣ ደራሲዋ በሕክምና ሙያ ላይ ያሉ ቢሆንም፣ ለመጽሐፉ ዝግጅት ሰፊ የታሪክ ምርምር ማድረጋቸው ተገልጿል። ታሪካዊ እውነታዎችን ከምናባዊ ትረካ ጋር በማዋሃድ የጸሐፌ ትዕዛዝን ስብዕና በቅርበት ለመረዳት ያስችላል።
መጽሐፉ ጸሐፌ ትዕዛዝ አክሊሉ በኤርትራ እና በሶማሊያ ጉዳዮች ላይ የነበራቸውን ሚና፣ የነበረባቸውን ከባድ ጭንቀት እና ለሀገር የከፈሉትን መስዋዕትነት ይዳስሳል።
እንዲህ ያሉ ሥራዎች ብሔራዊ ጀግኖችን በሕዝብ ልብ ውስጥ ዳግም ሕያው ለማድረግ እና ለትውልድ ለማስተዋወቅ ትልቅ ድርሻ እንዳላቸው ተጠቅሷል።
”ይህ መጽሐፍ አንባቢውን ወደ ኋላ በመውሰድ የወርቃማውን የኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ዘመን እንዲቃኝ የሚያደርግ ‘የታይም ማሽን’ (Time Machine) ነው” ሲሉ ረቂቁን ያረሙ ባለሙያዎች ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል።
የመፅሃፉ አርታኢ ቴዎድሮስ አጥላው እንደተናገረው ዶክተር ሰላማዊት ታደሠ ታሪካዊ ልቦለዱን ዕውነታውን መሠረት አድርጋ እንደፃፈችው እና የተዋጣላት መሆኑን መስክሯል ።
በምረቃው ወቅት እንደተገለጸው፣ መጽሐፉ ጸሐፌ ትዕዛዝ አክሊሉን እንደ አንድ ፖለቲከኛ ብቻ ሳይሆን እንደ አንድ ተራ ሰው፣ ወንድም እና ሀገር ወዳድ ዜጋ በቅርበት ለመረዳት አዲስ መስኮት ይከፍታል። በታሪኩ ውስጥ እንደ ሎሬንሶ ታዕዛዝ፣ ከተማ ይፍሩ እና ክፍሌ ወዳጆ ያሉ ሌሎች አንጋፋ ዲፕሎማቶችም ስም ተነስቷል።
መፅሀፉ 296 ገጾች ያሉት ሲሆን በ600 ብርም የሚሸጥ ነው።የምረቃው የሚድያ አስተባባሪ ተወዳጅ ሚድያ እና ኮምዩኒኬሽን (ዕዝራ እጅጉ) ነው።
