ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ሞቃዲሾ አዳን አብዱል አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ ፕሬዝዳንት ሀሰን ሼክ መሀሙድ አቀባበል እንዳደረጉላቸው የሶማሊያ የዜና ምንጮች ዘግበዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ እና ሶማሊያ በቱርክ አደራዳሪነት ውጥረት ለማርገብ ከተስማሙ ወዲህ ሞቃዲሾ ሲገቡ የዛሬው ለመጀመሪያ ጊዜ ነው።
በቆይታቸውም ከፕሬዝዳንት ሀሰን ሼክ መሃሙድ ጋር እንደሚመክሩ ይጠበቃል።
ኢትዮጵያ ባለፈው አመት ሶማሊያ እንደ ግዛቷ አካል ከምትቆጥራት ሶማሊላንድ ጋር የተፈራረመችውን የመግባቢያ ሰነድ የአዲስ አበባ እና ሞቃዲሾን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ማሻከሩ ይታወሳል።
ከአንድ አመት በላይ የዘለቀው ውጥረት በቱርክ አደራዳሪነት የሁለቱ ሀገራት መሪዎች በአንካራ ፊትለፊት ከተገናኙ በኋላ መርገቡም አይዘነጋም።
በአንካራው ስምምነት መሰረትም የሁለቱ ሀገራት ባለስልጣናት ባለፉት ወራት በሞቃዲሾ እና በአዲስ አበባ በመገናኘት ንግግር ሲያደርጉ ቆይተዋል።
