የጣሊያን መንግሥት በኢትዮጵያ የጤና ሥርዓት ግንባታን ለማገዝ እና የድንገተኛ አደጋ ሕክምና አገልግሎትን ለማጠናከር ከ260 ሺህ የአሜሪካ ዶላር በላይ የሚገመት የሕክምና መገልገያ መሣሪያዎች ድጋፍ አድርጓል።
የሕክምና መገልገያ ቁሳቁሶቹን የጤና ሚኒስትሯ ዶክተር መቅደስ ዳባ የተረከቡ ሲሆን፣ ልገሳው በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን የጠበቀ ወዳጅነት የሚያሳይና ኢትዮጵያ የጤና አገልግሎት ጥራትን ለማሻሻል የምታደርገውን ጥረት የሚደግፍ መሆኑን ገልጸዋል።
ሚኒስትሯ አክለውም መሣሪያዎቹ በሆስፒታሎች የሚሰጠውን ምርመራ የማድረግና ሕይወት የማዳን ተግባር ይበልጥ እንደሚያጠናክሩት አመልክተዋል።
በኢትዮጵያ የጣሊያን አምባሳደር ሴም ፋብሪ በበኩላቸው፣ ኢትዮጵያ የማርበርግ ቫይረስን በአጭር ጊዜ ውስጥ መቆጣጠር መቻሏን አድንቀው፣ ድጋፉ የሁለቱን አገራት የሁለትዮሽ ትብብር ይበልጥ እንደሚያጠናክረው ገልጸዋል።
የልገሳ ሥነ ሥርዓቱ የሁለቱን አገራት የቆየ ግንኙነት የሚያንጸባርቅ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅራቢ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር አብዱቃድር ገልገሎ ናቸው።
