የሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ከፈረንጆቹ 2011 ወዲህ ከፍተኛ የተባለለትን ወታደራዊ ጥሪ ለዜጎች አስተላልፈዋል፡፡
ፕሬዚዳንቱ ጥሪውን ያደረጉት ዕድሜያቸው ከ18 እስከ 30 ዓመት ለሚሆኑ 160 ሺህ የሀገሪቱ ወንዶች ሲሆን፣ ይህም የሀገሪቱን መከላከያ ሠራዊት አባላት ቁጥር በእጅጉ እንደሚያሰፋው ተገልጿል፡፡
ጥሪው የተላለፈው ፕሬዚዳንት ፑቲን የሩሲያን መከላከያ ሠራዊት አባላት ብዛት ወደ 2.39 ሚሊየን እንደሚያደርሱ ከተናገሩ ከወራት በኋላ መሆኑም ተጠቁሟል፡፡
ይህም በቀጣዮቹ ሦስት ዓመታት ውስጥ 180 ሺህ ተጨማሪ ኃይል ምልመላ ማለት ነው።
ምክትል አድሚራል ቭላድሚር ሲምልያንስኪ፣ አዲሶቹ ምልምል ወታደሮች በዩክሬን ጦርነት እንደማይሳተፉ አረጋግጠዋል።
ይሁን እንጂ ከዚህ በፊት ሰራዊቱን የተቀላቀሉ ምልምል ወታደሮች በዩክሬን ጦርነት ተሳትፈው ህይወታቸው ያለፈ ስለመኖሩ በዩክሬን በኩል መነገሩ ተነስቷል፡፡
ፕሬዚዳንት ፑቲን ክስተቱን አስመልክተው በሰጡት ማስተባበያ፣ ጅምር ላይ ጥቂት ምልምል ወታደሮችን በስህተት ወደ ግንባር በመላክ የተፈጠረ እንጂ ሁሉንም ያሳተፈ እንዳልነበር መግለፃቸውን የአር ቲ ኢ ዘገባ አመልክቷል፡፡
