የቀድሞው የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ጌታቸው ረዳ የሚመሩት የሕወሓት ክንፍ፣ ራሱን የቻለ የፖለቲካ ፓርቲ ለመኾን ዝግጅት እያደረገ እንደሚገኝ አስታውቋል። ቡድኑ ወደ አንድ ፓርቲነት ለመቀየር የወሰነው፣ ለትግራይ የወደፊት ሰላማዊና ዲሞክራሲያዊ ዕጣ ፋንታ ለመታገል እንደኾነ ገልጧል።
ቡድኑ፣ ደብረጺዮን ገ/ሚካኤል የሚመሩት የሕወሓት ክንፍ በጊዜያዊ አስተዳደሩ እገዛ የማዕድን ዘርፉንና የትግራይ ልማት ማኅበርን ጨምሮ የትግራይ ቁልፍ ተቋማትን በብቸኝነት በመቆጣጠር ላይ ይገኛል ብሏል።
ሲቪል ማኅበራት ድርጊቱን ለማስቆም በፍርድ ቤት ጭምር እንቅስቃሴ እንዲጀምሩ የጠየቀው ቡድኑ፣ የደብረጺዮን ቡድን ቁልፍ ተቋማትን እንዲቆጣጠር ጊዜያዊ አስተዳደሩ ለቡድኑ ይሠጠዋል ያለውን ድጋፍ እንዲያቆምም ጠይቋል። የጌታቸው ቡድን ይህን እንቅስቃሴ መጀመሩ የተሠማው፣ ምርጫ ቦርድ የሕወሓትን ሕጋዊነት እሠርዛለሁ ያለበት ቀነ ገደብ ሊጠናቀቅ ሁለት ሳምንት በቀረው ሰዓት ላይ ነው።
[ዋዜማ]
