ከዓለም ጤና ድርጅት (WHO) ለኬንያ ተረጂዎች ብቻ እንዲያገለግል የተሰጠ “ፕላምፒነት” የተሰኘ አልሚ ምግብ፤ ኢትዮጵያ ውስጥ ሲሸጥ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር መዋሉን የአዲስ አበባ ከተማ ምግብና መድኃኒት ባለሥልጣን ለአሐዱ አስታውቋል።
አልሚ ምግቡ ከኬንያ ተነስቶ ኢትዮጵያ የገባው በመድኃኒትነት ተመዝግቦ መሆኑ ታውቋል፡፡
በባለሥልጣን መሥሪያ ቤቱ የምግብና ጤና ነክ ተቋማት ቁጥጥር ዳይሬክተር እስጢፋኖስ ጌታቸው ለአሐዱ እንደገለጹት፤ ለኬንያ ተብሎ የተሰጠን አልሚ ምግብ ወደ ኢትዮጵያ በማስገባት፣ በአዲስ አበባ ከተማ በመርካቶ አካባቢ በተደረገ ክትትል፣ ፕላምፒነቱ በቅርቡ ሙሉ በሙሉ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ሊውል ችሏል ተብሏል።
በዚህም ፕላምፒነት ወደ ሀገር ውስጥ ሲገባ ተመዝግቦ በመሆኑና ለአንዱ ሀገር የተሰጠው አልሚ ምግብ ወይም “ፕላምፒነት” ከሌላኛው ሀገር ጋር ተመሳሳይ ባለመሆኑ ከሀገር ሀገር ማንቀሳቀስ እንደማይቻል ዳይሬክተሩ ተናግረዋል።
“ፕላምፒነት” የተሰኘው አልሚ ምግብ በየትኛውም ቦታ ሊሸጥ የማይችልና ለእርዳታ አገልግሎት ብቻ የሚውል አልሚ ምግብ እንደሆነ ያብራሩት ዳይሬክተሩ፤ ማኅበረሰቡ በምግብ እጥረት ለተጎዱ ወገኖች የሚውለውን አልሚ ምግብ ሲሸጡ የተመለከታቸውን በ8864 በመደወል ጥቆማ እንዲሰጥም ጥሪ አቅርበዋል፡፡
