በጤናው ዘርፍ ከ4.5 ሚሊዮን በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ የሚያደርገው የክረምት በጎ አድራጎት ትግበራ ነፃ የጤና ምርመራ እና ህክምና አገልግሎት ዛሬ በይፋ ተጀምሯል፡፡
የጤና ሚኒስቴር ዶ/ር መቅደስ ዳባ እና ሌሎች አመራሮች በተገኙበት በይፋ የተጀመረው የ2017 ዓ.ም የጤናው ዘርፍ የክረምት በጎ አድራጎት ትግበራ ከፍለው መታከም የማይችሉ ከ4.5 ሚሊዮን በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ነጻ የጤና ምርመራና ህክምና አገልግሎትን ያካትታል፡፡
የዘንድሮው ነጻ የጤና ምርመራና ህክምና አገልግሎት ‘በመትከል ማንሰራራት›› በሚል መሪ ሀሳብ በአገር አቀፍ ደረጃ በስፋት እንደሚካሄድ የጤና ሚኒስትሯ ዶ/ር መቅደስስ ዳባ የበጎ ፍቃድ አገልግሎቱን ባስጀመሩበት ወቅት ገልጸዋል።
መርሃ ግብሩ በጤና ተቋማት ብልሽት ገጥሟቸው አገልግሎት የማይሰጡ የህክምና መስጫ መሳሪያዎችን የመጠገን፤ በኢትዮጵያ የሚገኙ ለህክምና የሚያገለግሉ ዕጽዋትን የመትከል መርሃ ግብር የሚያጠቃልል መሆኑን ዶ/ር መቅደስ ዳባ ተናግረዋል።
ህብረተሰቡም እንደ ዋነኛ ባለድርሻ አካል የአገልግሎቱ ተጠቃሚ በመሆን የጤና ቅድመ ምርመራና ህክምና እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበው፤ ለበጎ ተግባር መሳካት ዋነኛ አካል ለሆኑት የጤና ባለሙያዎችም ምስጋና አቅርበዋል።
ሌሎች ባለድርሻ አካላት የድርሻውን እንዲወጡም ጠይቀዋል፡፡
የአለርት ኮምፕርሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ዋና ስራ አስኪያጅ ዶ/ር ሽመልስ ገዛኸኝ በበኩላቸው፤ ሆስፒታሉ የተለያየ አይነት ምርመራ እና ህክምና አገልግሎት ለመስጠት ማቀዱን ገልጸው፤ የችግኝ ተከላ፣ የአካባቢ ጽዳት፣ የመማሪያ ቁሳቁስ ድጋፍ በመርሀግብሩ የተካተቱ ተግባራት መሆናቸውን ገልጸዋል።
በጤና ሚኒስቴር አስተባባሪነት የ2017 ዓ.ም የነጻ ጤና ምርመራ እና ህክምና አገልግሎት በአገር አቀፍ ደረጃ ማስጀመርያ መርሀ ግብር በአለርት ኮምፕርሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል የተጀመረ ሲሆን ሌሎች ባለድርሻ አካላትንም በማስተባበር ሙሉውን ክረምት የሚቆይ ይሆናል።
