ታይም መፅሔት የዓመቱ ምርጥ ልጅ በሚል በፊት ገጹ አትሞታል። በርካታ ዓለም ዓቀፍ መገናኛ ብዙኃንም አዳጊው ሳይንቲስት በሚል ሰፊ የዘገባ ሽፋን ሰጥተውታል። ሔማን በቀለ ወንድወሰን ሙሉ ስሙ ነው።
በአዲስ አበባ የተወለደው ሔማን በአራት ዓመቱ ነበር ወደአሜሪካ ቨርጂኒያ ከቤተሰቡ ጋር ያቀናው። እናቱ ወይዘሮ ሙሉእመቤት ጌታቸው መምህር ሲሆኑ፤ አባቱ ደግሞ በዩኤስኤአይዲ የሰው ሃብት ባለሙያ ናቸው።
የሳይንስ ፍላጎቱ በልጅነቱ የሰረጸበት ሔማን ገና 7 ዓመት ሳይሞላው ነበር ቤት ውስጥ ያገኛቸውን ጎጂ ያልሆኑ ኬሚካሎች በማዋሃድ መመራመር የጀመረው።
የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን በሮበርት ፎረስት የተከታተለው አዳጊው፤ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ደግሞ በካርተር ጂ ዉድሰን እየተከታተለ ይገኛል።
በትምህርት ቤቱ ላብራቶሪዎች የተሻሻሉ ዕውቀቶችን እያገኘ ያደገው ሔማን፤ በ11 ዓመቱ የቆዳ ካንሰር ላይ ያተኮረ ምርምርን ማድረግ እንደጀመረ ግለ ታሪኩ ያስረዳል።
በኢትዮጵያ የሚያጋጥመው ለፀሐይ ብርሃን ጨረራ በስፋት የመጋለጥ ችግርን መገንዘቡ ለምርምር ሀሳቡ መነሾ እንደሆነው አዳጊው ሳይንቲስት ይገልጻል። ይህንን ችግር ለመፍታት ደግሞ በሳሙና መልክ የሚዘጋጅ ሕክምናን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል የምርምር ሃሳብ ነድፎ ወደ ስራ መግባቱን ነው የሚያስረዳው።
ሃሳቡንም 3 ኤም የወጣቶች ዓለም አቀፍ የሳይንስ ውድድር ላይ አቅርቦ እ.አ.አ በ2023 ተቀባይነትን በማግኘቱ አሸናፊ መሆን ችሏል። ውድድሩን በማሸነፉም ለስራው የሚያግዙት ከፍተኛ ሳይንቲስቶችን አግኝቷል።
በውድደሩ አሸናፊ በመሆኑ ያገኘውን 25 ሺህ ዶላር ለቀጣይ የምርምር ስራዎቹ ያዋለው አዳጊው፤ ጥረቱን በማጠናከርም የቆዳ ካንሰርን የሚያክም ሳሙና በማዘጋጀት ካንሰርን በማከም ረገድ ከፍተኛ ውጤት የታየበትን ምርምር አፍልቋል።
ይህ ለቆዳ ካንሰርን ሕክምና የሚውለው ሳሙና አቅምን ባገናዘበ መልኩ ለበርካቶች ተደራሽ ለማድረግ ዓላማ እንዳለው በአንድ ወቅት ለሲኤንኤን ተናግሯል። የ15 ዓመቱ ታዳጊ በምርምር ሥራው አማካኝነት ለጀግና ወጣቶች የሚበረከተውን የግሎሪያ ባሮንን ሽልማት አግኝቷል።
የዓመቱ የአሜሪካ የዓመቱ ምርጥ ታዳጊ ሳይንቲስት የሚል ስያሜም ተሰጥቶታል። በአሁኑ ወቅት በጆን ሆፕኪንስ ዩኒቨርሲቲ ተጨማሪ ምርምር እያደረገ ይገኛል።
ሔማን ለምርምር ውጤቱ ከአሜሪካን የምግብና መድኃኒት አስተዳደር (FDA) ዕውቅና ማግኘትና እ.አ.አ እስከ 2028 ድረስ ምርቱን በዓለም አቀፍ ደረጃ ለማሰራጨት የሚያስችል ለትርፍ ያልተቋቋመ ድርጅት ማቋቋምን አቅዶ እየሰራ ይገኛል።
ይህን ይበል የሚያሰኝ ምርምሩን በተመለከተም በበርካታ ዓለም አቀፍ ግዙፍ መድረኮች ላይ ቀርቦ ገለጻ እያደረገ የሚገኘው ትውልደ ኢትዮጵያዊው፤ ለበርካታ ታዳጊዎች ዓርዓያ የሚሆን ሥራ እያከናወነ ነው።
እሱንና ሁለት እህቶቹን በትችላላችሁ መንፈስ ያሳደጉ ቤተሰቦቹን ያመሰገነው ሔማን፤ ነገ የተሻለ ነው ሲል ይገልጻል።
